የአረንጓዴ አሻራ ሌጋሲ ጠፍቶ የነበረውን የሐረማያ ሃይቅ የመለሰ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ

80

ነሐሴ 07 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአረንጓዴ አሻራ ሌጋሲ ጠፍቶ የነበረውን የሐረማያ ሃይቅ የመለሰ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ተናገሩ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በሐረር ከተማ አረንጓዴ አሻራቸውን በዛሬው ዕለት አኑረዋል ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በከተማው በተለምዶ ሃማሬሳ በሚባለው የሐረሪ ባህል ማዕከል ቅጥር ግቢ ውስጥ ነው ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን ያኖሩት።

ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ አቶ አገኘሁ ተሻገር፣ አቶ አደም ፋራህ ፣ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪና ሌሎች የፌደራልና የክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት፣የሐረሪ ክልል የምክር ቤት አባላት፣የሃይማኖት አባቶች፣የአገር ሽማግሌዎችና አባገዳዎችም ችግኝ ተክለዋል።

በመርሃ ግብሩ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተናገሩት የአረንጓዴ አሻራ ሌጋሲ ጠፍቶ የነበረውን ሃይቅ የመለሰ ነው።"ለዚህም ከሐረርጌ ህዝብ በላይ ለዚህ ምስክርነት የሚሆን የለም " ብለዋል።

"ባለፉት 4 ዓመታት በተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ሌጋሲ በአካባቢው ጠፍተው የነበሩ ሃይቆች ተመልሰዋል፤ ምርትና ምርታማነት ጨምሯል" ሲሉም ተናግረዋል።

የአካባቢው ማህበረሰብ እና አርሶ አደሩ የጀመረውን የአረንጓዴ አሻራና ምርትና ምርታማነትን የማጎልበት ስራ አጠናክሮ እንዲቀጥል መልዕክት አስተላልፈዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም