የደቡብ ክልል ምክር ቤት ለ2015 ከ46 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ በጀት አፀደቀ

207

ሐምሌ 15 ቀን 2014 (ኢዜአ) የደቡብ ክልል ምክር ቤት ባካሄደው ጉባኤ ለ2015 ዓም 46 ቢሊየን 316 ሚሊየን 524 ሺ ብር በጀትን በሙሉ ድምጽ አፅድቋል፡፡

ምክር ቤቱ የቀረበለትን በጀት መርምሮ ዛሬ ያጸደቀው እያካሄደ ባለው 6ኛ ዙር 1ኛ አመት የስራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባኤው ነው።

የፀደቀው በጀት የክልሉ መንግስት በ2015 ለሚያከናውናቸው የተለያዩ የልማት ስራዎችና አገልግሎት ዘርፎች የሚውል እንደሆነ ተገልጿል።

ከበጀቱ ውሰጥ የክልል ማእከል ድርሻ 18 ፐርሰንት ሲሆን ቀሪው ደግሞ የዞኖችና ልዩ ወረዳዎች የተደለደለ መሆኑም በጉባዔው ላይ ተመላክቷል።

የበጀት ድልድሉ የተጀመረውን እድገት ለማስቀጠል እና በኢኮኖሚው ውስጥ መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት ወሳኝ የሆነውን የማኑፋክቸሪንግ የኢንዱስትሪ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያስችላል ተብሏል።

በተለይ በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ በሜካናይዜሽንና ኩታ ገጠም እርሻ፣ የበጋ መስኖ ስንዴና የአትክልትና ፍራፍሬ ልማትን ጨምሮ አነስተኛ ፣መካከለኛና ከፍተኛ መስኖ ጥናትና ግንባታ ስራዎችን ለማሳለጥ ታሳቢ በማድረግ የበጀት ድልድሉ መደረጉንም ምክር ቤቱ አስታውቀዋል።

ኢትዮጵያን እናልማ፣እንገንባ፣እንዘጋጅ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም