በኢትዮጵያ እና አሜሪካ መካከል ያለው የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነት በባህል ልውውጥ ተጠናክሮ ይቀጥላል

111

ሰኔ 9 ቀን 2014 (ኢዜአ)በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ዶክተር ኢንጅነር ስለሺ በቀለ በኢትዮጵያ እና አሜሪካ መካከል ያለው የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነት በባህል ልውውጥም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጹ።

አምባሳደር ዶክተር ኢንጅነር ስለሺ በቀለ ይህን ያሉት ከቀድሞው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር አምባሳደር ቲቦር ናጊ ጋር በተወያዩበት ወቅት ነው።

አምባሳደሩ ለቀድሞው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር እና ከቴክሳስ ቴክ ዩኒቨርሲቲ እና ከአንጀሎ ስቴት ዩኒቨርሲቲ ለተውጣጡ 15 ተማሪዎች በኢትዮጵያ እና አሜሪካ መካከል ስላለው የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነት ገለፃ አድርገዋል።

ተማሪዎቹ ጋር ከተደረጉላቸው ውይይቶች በተጨማሪ የኢትዮጵያን ባህላዊ የቡና ስነ ስርዓት የመታደም እድል አግኝተዋል።

የተማሪዎቹ የጉብኝት መርሃ ግብር በሁለቱ አገራት መካከል የጋራ መግባባትን ለማጎልበት፣የባህል ልውውጥ ለማጎልበት እና ወዳጅነተን ለማጠናከር እንደሚረዳ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም