ኢትዮጵያና ጣልያን ያላቸውን ሁለትዮሸ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ይሰራሉ--የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች

91

ሰኔ 6 ቀን 2014 (ኢዜአ) ኢትዮጵያና ጣልያን ያላቸውን ሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩ የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች አረጋገጡ፡፡

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የጣሊያን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሊውጂ ዲ ማዮን በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል፡፡

ውይይቱን ተከትሎም ሁለቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

አቶ ደመቀ መኮንን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በውይይታቸው በዋናነት በሁለትዮሽ፣ቀጠናዊና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን ተናግረዋል፡፡

ሁለቱ አገራት ረዥም ዘመናትን ያስቆጠረ ጠንካራ ግንኙነት እንዳላቸው ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ይህ ግንኙነት ይበልጥ እንዲጠናከር ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል፡፡

የጣሊያን መንግሥት በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ የሚያራምደውን ሚዛናዊ አቋምም አድንቀዋል፡፡

በተመሳሳይ የጣሊያን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሊውጂ ዲ ማዮ አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም