በከሚሴ ከተማ የተጀመረውን ህግ ማስከበር ዘመቻ የሚደግፍና አሸባሪው ሸኔን የሚያወግዝ ሰልፍ እየተካሄደ ነው

136

ከሚሴ፤ ግንቦት 30 ቀን 2014 (ኢዜአ) በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሄረሰብ ዞን አስተዳደር ከሚሴ ከተማ የተጀመረውን ህግ ማስከበር ዘመቻ የሚደግፍና አሸባሪውን ሸኔን የሚያወግዝ ሰልፍ እየተካሄደ ነው፡፡

በሰልፉ ከከሚሴ ከተማ ነዋሪዎች በተጨማሪ አጎራባች ወረዳዎች ነዋሪዎችም እየተሳተፉ ነው፡፡

በሰልፉ ላይ “የተጀመረውን ህግ ማስከበር ዘመቻ እንደግፋለን፣ ወንጀለኛን አንተባበርም፣ ከመንግስት ጎን ነን፣ አሸባሪው ሸኔ ታሪካዊ ጠላታችን ነው፣ ሸኔን አንታገስም፣ የሸኔን አከርካሪ በጋራ እንሰብረዋለን፣ ህግ ይከበር፣ ኢትዮጵያ ትቀጥላለች፣ አንድነታችንና ሰላማችንን በጋራ እንጠብቃለን፣ በተላላኪዎች አንድነታችን አይፈርስም” የሚሉና ሌሎች መልዕክቶችም እየተላለፉ ነው፡፡

May be an image of one or more people, people standing and sky

የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን መንግስት ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ጀማል ሐሰን ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደገለጹት ህብረተሰቡ በራሱ ፍላጎት በነቂስ ወጥቶ ህግ ማስከበር ዘመቻውን ከመደገፍ ባለፈ አሸባሪው ሸኔን እያወገዘ ነው፡፡

የሰልፉ ዓላማም የህግ የበላይነት እንዲከበር የተጀመረውን ዘመቻ መደገፍና የህዝብ ጠላት የሆነውን አሸባሪው ሸኔን ማውገዝና በቅንጅት ማጥፋት ነው ብለዋል፡፡

ህብረተሰቡ ከዚህ በፊት የህግ የበላይነት ይከበር በሚል መንግስትን በተደጋጋሚ ሲጠይቅ እንደነበረ አስታውሰው፤ በተጀመረው ህግ ማስከበር ዘመቻ በዞኑ ሰላም በመስፈኑ ህብረተሰቡ በነጻነት መንቀሳቀስ ጀምሯል ብለዋል፡፡

በርካታ በነፍስ ማጥፋት ወንጀል የሚጠረጠሩ ግለሰቦች፣ዘራፊዎች፣ የአሸባሪው ሸኔ አባላት፣ ህገ ወጥ የመሳሪያ አዘዋዋሪዎችና ሌሎች ወንጀለኞችም በህግ ስር እየዋሉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ተመሳሳይ ሰላማዊ ሰልፍ በዞኑ ባቲና ሰንበቴ ከተሞችም እየተካሄደ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም