የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር ሀብታሙ የቦንጋ ከተማ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክትን ጎበኙ

211

ግንቦት 23 ቀን 2014 (ኢዜአ)  የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር ሀብታሙ ኢተፋ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና ከተማ ቦንጋ እየተገነባ ያለውን የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ጎበኙ።

ጉብኝቱ በክልሉ በግንባታ ሂደት የሚገኙ የንፁህ ውሃ መጠጥ ፕሮጀክቶችን አፈፃፀም ላይ ውይይት ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።

ሚኒስትሩ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና ከተማ ወደ ሆነችው የቦንጋ ከተማ ሲደርስ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾን ጨምሮ የተለያዩ የስራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውላቸዋል።

ከፍተኛ ዝናብ በማይለየው ካፋ ዞን የምትገኘው ቦንጋ ከተማ በንፁህ መጠጥ ውሃ እጦት ተደጋጋሚ ቅሬታ ከሚቀርብባቸው ከተሞች አንዷ ናት።

ለችግሩ ዕልባት ለመስጠት የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት በመተግበር ላይ ሲሆን፤ በውይይቱም በፕሮጀክቱ በአፈፃፀም ላይ ላጋጠሙ ችግሮች ውሳኔዎች ይቀመጣል ተብሎ ይጠበቃል።  

በተመሳሳይ ሚኒስቴሩ ለመስክ ስራ የሚውሉ አራት የሞተር ሳይክሎች እና 10 ላፕቶፕ ኮምፒተሮች ድጋፍ አድርጓል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም