መኮንኖች ኢትዮጵያዊ ጀግንነት፣ከሀገር ፍቅርና ከህገመንግስቱ የሚቀዳ አላማና ሁለገብ እውቀት ሊኖራቸው ይገባል - ኢዜአ አማርኛ
መኮንኖች ኢትዮጵያዊ ጀግንነት፣ከሀገር ፍቅርና ከህገመንግስቱ የሚቀዳ አላማና ሁለገብ እውቀት ሊኖራቸው ይገባል
ግንቦት 21 ቀን 2014 (ኢዜአ)የሀገር መከላከያ ሰራዊት መኮንኖች ኢትዮጵያዊ ጀግንነት፣ከሀገር ፍቅርና ከህገመንግስቱ የሚቀዳ አላማና ሁለገብ እውቀት ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ዐቢይ አሕመድ ገለጹ።
የኢትዮጵያ ወታደራዊ አካዳሚ 69ኛ ዙር የጥቁር አንበሳ ኮርስ የሲቪል ወታደራዊ መኮንኖችን በምክትል መቶ አለቃ ማዕረግ አስመርቋል።
በመርሀ ግብሩ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ዐቢይ አሕመድ፣የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች ተገኝተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልእክት የሀገር መከላከያ ሰራዊት መኮንኖች ኢትዮጵያዊ ጀግንነት፣ከሀገር ፍቅርና ከህገመንግስቱ የሚቀዳ አላማና ሁለገብ እውቀት ሊኖራችሁ ይገባል ብለዋል።
የነገ የሀገር ኩራት ጀነራሎችና ሀገር መሪዎች መሆናችሁን በቅጡ በመረዳት ለአላማችሁ የምትታትሩ፣የምትተጉና ከቀድሞ የጦር መሪዎች ተምራችሁ የምትሰሩና የምታሰሩ መሆን ይጠበቅባችኋል ሲሉ አሳስበዋል።
የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ፤ የዛሬ ተመራቂዎች የተሰጣቸውን ስልጠና በብቃት በመወጣት የመከላከያ ሰራዊት አባል መሆን የቻሉ መኮንኖች መሆናቸውን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ችግር ውስጥ በገባችበት ወቅት ሀገራቸውን አስቀድመው በአስቸጋሪና ውስብስብ ስልጠና ተፈትነው ያለፉና ለምረቃ የበቁ መኮንኖች መሆናቸውንም ጠቅሰዋል።
የ69ኛ ተመራቂ መኮንኖች አብዛኞቹ የመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩበት ስራቸውን አቁመው በራሳቸው ተነሳሽነት እናት ሀገር ጥሪን ተቀብለው ሰራዊቱን የተቀላቀሉ ናቸው።