በቀጣዩ አንድ ሳምንት በአብዛኛው የኢትዮጵያ ክፍል ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ይጠበቃል - ኢዜአ አማርኛ
በቀጣዩ አንድ ሳምንት በአብዛኛው የኢትዮጵያ ክፍል ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ይጠበቃል

ግንቦት 17 ቀን 2014 (ኢዜአ) በአብዛኛው የኢትዮጵያ ክፍል በቀጣዩ አንድ ሳምንት ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ የሚጠበቅ መሆኑን የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው ባለፉት አስር ቀናት በምዕራብ ወለጋ ቄሌም፣ የተወሰኑ የኢሉባቦራ ዞኖች መደበኛ ዝናብ የነበራቸው መሆኑን ጠቅሷል።
በመጪው አንድ ሳምንት ደግሞ ከክረምት ወቅት መጀመር ጋር ተያይዞ በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል ከቀላል እስከ መካከለኛ ዝናብ ይኖራቸዋል ብሏል።
በተለይ በምዕራብ ና የደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከኛ ዝናብ እንደሚጠበቅም በመግለጫው ተመልክቷል።
በአማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም፣ ምዕራብ ጎንደር ዞኖች፣ አዊ ዞን፣ በኦሮሚያ ጅማ ኢሉአባቦራና ሁሉም የወለጋ ዞኖች ደረቅ የአየር ሁኔታ ይኖራቸዋል።
በተጨማሪም የጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ ዞኖች፣ የደቡብ ምዕራብና የሲዳማ ሁሉም ዞኖች፣ ደቡብ ኦሞ ኮንሶን ጨምሮ የተወሰኑ አካባቢዎች ተመሳሳይ የአየር ሁኔታ ሊኖራቸው እንደሚችል ተገምቷል።
በምስራቅ ሀረርጌ፣ አርሲ፣ ባሌና ምስራቅ ባሌ እንዲሁም የተወሰኑ የጉጂ ዞኖች ደግሞ ከቀላል እስከ መካከለኛ ዝናብ ሊያገኙ ይችላሉ ብሏል የኢንስቲትዩቱ መግለጫ።
ኦሞጊቤ፣ አባይ፣ ባሮአኮቦ የመካከለኛው የታችኛው ስምጥ ሸለቆ የታችኛውና መካከለኛው የተከዜ የላይኛውና የመካከለኛው ገናሌዳዋ ተፋሰሶች እስከ ከፍተኛ እርጥበት የሚያገኙ ሲሆን በጥቂት ቦታዎች ከባድ ዝናብ ሊኖር እንደሚችልም ጠቁሟል።
በተለይ ባሮአኮቦ የታችኛው አባይ፣ እንዲሁም ኦሞ ጊቤ ተፋሰሶች ላይ ቅጽበታዊ ጎርፍ ሊኖር ስለሚችል ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ አመላክቷል።
ኢትዮጵያን እናልማ፣እንገንባ፣እንዘጋጅ

ሀገርን በዘላቂነት እናልማ

የፈረሰውን አብልጠን እንገንባ

ለማንኛውም ፈተና እንዘጋጅ
