የቻይናው ሳውዝዌስት ፋርማሲዩቲካል ኩባንያ ልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ ጉብኝት ሊያደርግ ነው

91

ግንቦት 17 ቀን 2014 (ኢዜአ) የቻይናው ሳውዝዌስት ፋርማሲዩቲካል ኩባንያ ልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ የቅድመ-ኢንቨስትመንት ጉብኝት እንደሚያደርግ ተገለጸ።

ኢትዮጵያ በመድኃኒት ምርትና ማከፋፈል ኢንዱስትሪ ለሚሰሩ የውጭ ኩባንያዎች የተለዩ ቦታዎችን ማዘጋጀቷም ተነግሯል።

በቻይና ምክትል የኢትዮጵያ ሚሲዮን መሪ አምባሳደር ዳዋኖ ከድር ከሳውዝዌስት ፋርማሲዩቲካል ኩባንያ ዋና ዳይሬክተር ያ ዢያን ጋር ኩባንያው በኢትዮጵያ መዋዕለ ነዋዩን ማፍሰስ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ማድረጋቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

በኢትዮጵያ የመድኃኒት ምርትና ማከፋፈል(ፋርማሲዩቲካል) ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ የውጭ ኩባንያዎች ብቻ የተለዩ ቦታዎች መዘጋጀታቸውንና የገበያ አማራጮችና እድሎች መመቻቸታቸውን አምባሳደር ዳዋኖ ገልጸዋል።

የኩባንያው ኃላፊ በኢትዮጵያ የቅድመ-ኢንቨስትመንት ጉብኝት በማካሄድ ኢትዮጵያ ያላትን የገበያ አማራጭ እንዲመለከቱም ጥሪ አቅርበዋል።

የሳውዝዌስት ፋርማሲዩቲካል ኩባንያ ዋና ዳይሬክተር ያ ዢያን ከኩባንያቸው የተውጣጣ ከፍተኛ የልዑካን ቡድን መርተው በኢትዮጵያ የቅድመ ኢንቨስትመንት ጉብኝት እንደሚያካሄዱ ቃል መግባታቸውን ከቃል አቀባይ ጽህፈት ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

ኢትዮጵያና ቻይና በቅርቡ በኢንቨስትመንት መስክ መስራት የሚያስችላቸውን ስድስት የተለያዩ ስምምነቶችን መፈራረማቸው የሚታወስ ሲሆን፤ስምምነት ከተደረገባቸው መስኮች አንዱ የመድኃኒት ምርትና ማከፋፈል(ፋርማሲዩቲካል) አንዱ ነው።

ኢትዮጵያን እናልማ፣እንገንባ፣እንዘጋጅ 

‼️

ሀገርን በዘላቂነት እናልማ

‼️

የፈረሰውን አብልጠን እንገንባ

‼️

ለማንኛውም ፈተና እንዘጋጅ

‼️
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም