አክራሪነትንና ፅንፈኝነትን ለሚያራምዱ ፀረ-ሰላም ቡድኖች አጀንዳ መጠቀሚያ አንሆንም...የሀዋሳ ከተማ ወጣቶች

99

ሀዋሳ፤ ግንቦት 7/204 (ኢዜአ)፡አክራሪነትንና ፅንፈኝነትን የሚያራምዱ ፀረ-ሰላም ቡድኖች አጀንዳ መጠቀሚያ እንደማይሆኑና እኩይ ዓለማቸውንም እንደሚያመክኑ የሀዋሳ ከተማ ወጣቶች አስታወቁ።

ከወጣቶቹ መካከል ወጣት  መላኩ ሴካ ለኢዜአ እንደገለጸው  ፅንፈኝነትና አክራሪነትን የሚያራምዱ ፀረ-ሰላም ቡድኖች ወጣቶችን የአጀንዳቸው መጠቀሚያ ለማድረግ እየሰሩ ነው።

ወጣቱ የሀገሩን አንድነትና ሰላም ለመጠበቅ በአካባቢው ከሚያደርገው ጥረት ባለፈ ግንባር ድረስ በመዝመትም ለሀገሩ ያለውን ጥልቅ ፍቅር በትግባር ማሳየቱን አስታውሶ፤ፀረ-ሰላም ቡድኖች  በፅናት መታገል ይገባል።

የአብሮነት እሴቶቻችን ላይ ማተኮር ይገባል ያለው ወጣቱ፤  ''የኃይማኖት አባቶችን ምክር በመስማት ለዘመናት የኖርንበትን የኃይማኖት እኩልነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል'' ብሏል።

ወጣት ትሸጋገር ግርማ በበኩሏ በሀገር ግንባታ ሂደት የወጣቱ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ጠቅሳ፤ ለአብሮነትና ለአንድነት መጠናከር እያደረገ ያለውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስባለች።

ኃይማኖትን ሽፋን አድርገው የሚንቀሳቀሱ ፀረ-ሰላም ቡድኖች ወጣቱን የአጀንዳቸው መጠቀሚያ እንዳያደርጉ በንቃት መከታተል እንደሚገባም አስገንዝባለች።

ከውስጥም ከውጭም የሚገጥሙ ችግሮችን በሃሳብ የበላይነትና ምክንያታዊ በሆነ መልኩ መፍታት እንደሚገባ ገልፃ  የሚጠበቅባትን ለመወጣት  ዝግጁ መሆኗን አአረጋግጣለች።

ብዝሃነትን በያዘች ሀገር ውስጥ እንደሚኖር ወጣት ችግሩን ማብረድ እንጂ የችግሩ አባባሽ መሆን ተገቢ አለመሆኑንም ተናግራልች።

በሁሉም ኃይማኖቶች አስተምሮ የሚሰብከው ሰላም መሆኑን ገልጻ፤በተለያዩ ኃይማኖት ተከታዮች መካከል ያለው የእርስ በርስ መከባበር እንዲጠናከር የኃይማኖት አባቶች ምዕመናን ማስተማርና መገሰፅ እንዳለባቸውም ተናግራለች።

ወጣቱ ለሀገር ሁለንተናዊ ልማትና ዕድገት እንተጋ ወጣት ተኮር የሰላም እሴት ግንባታ ላይ መስራት ያስፈልጋል ያለው ደግሞ ወጣት በቃሉ መሰረት ነው።

ነገሮችን በተገቢው መቃኘት የሚችል ስብዕናው የተስተካከለ ወጣት ለየትኛውም አፍራሽ ኃይል አጀንዳ መጠቀሚያ አይሆንም ብሏል።

ለምን? የሚል ወጣት እንዲፈጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የበኩሉን ድርሻ እያበረከተ መሆኑንም ተናገሯል።

ወጣት አየለ ሳጋቶ በበኩሉ ወጣቱ በሀገራዊ ጉዳይ ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብሏል።

በማህበራዊ ሚዲያ  የሚለቀቁ የተሳሳቱና ሀገርን ሊያፈርሱ የሚችሉ አስተሳሰቦችን መመከት እንደሚገባ  አስገንዝቧል።

በኃይማኖት ሽፋን ተከባብሮ የኖረውን ህዝብ ለማጋጨት የሚሰሩ ፀረ-ሰላም ቡድኖችን እኩይ ዓላማ ማምከን የወጣቱ ሚና መሆን አለበትም ብል።

''የትኛውም ኃይማኖት የፀብ አስተምሮ የለውም'' ያለው ወጣቱ ህዝብ ከህዝብ ሊያጋጩ የሚችሉ ጉዳዮችን አስቀድሞ በመከላከል የድርሻውን እንደሚወጣ ተናግል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም