የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ሙያዊ ስነ-ምግባርን ባከበረ መልኩ የፕሬስ ነጻነትን በአግባቡ መጠቀም አለባቸው

119

ግንቦት 01 ቀን 2014 (ኢዜአ) የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ሙያዊ ስነ-ምግባርን ባከበረ መልኩ የፕሬስ ነጻነትን በአግባቡ መጠቀም እንዳለባቸው ተጠቆመ፡፡

የዓለም የፕሬስ ነጻነት ቀን ለ31ኛ ጊዜ “ጋዜጠኝነት በዲጂታል ዓለም ውስጥ” በሚል መሪ ሃሳብ በኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ምክር ቤት እና በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት ቢሮ አስተባባሪነት ተከብሯል፡፡

በመርሃ ግብሩም ጋዜጠኞች የፕሬስ ነጻነቱን ለድርድር ሳያቀርቡ ሙያዊ ስነ-ምግባር ባከበረ መልኩ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ሰብሳቢ ጋዜጠኛ አማረ አረጋዊ በዚሁ ወቅት ፤ የፕሬስ ነጻነት መከበሩ መንግስታት ለፕሬስ ነጻነት የገቡትን ቃል እንዲያከብሩና ጋዜጠኞች ስራቸውን ስነ-ምግባር ባከበረ መልኩ እንዲያከናውኑ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡      

እንዲሁም በስራቸው ምክንያት የህይወት መስዋዕትነት የከፈሉት ጋዜጠኞችም የሚታሰቡበት እለት ጭምር መሆኑንም ገልጸዋል፡፡  

የፕሬስ ነጻነት ቀን ሲከበር በተለይ የዲጂታል ሚዲያ ባለሙያዎች ከጥላቻ በራቀ መልኩ ስራቸውን በኃላፊነት እንዲሰሩ ግንዛቤ በመፍጠር ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡

የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት የኢትዮጵያ ተወካይ ዩሚኮ ዩኮዞኪ በበኩላቸው መረጃ እና ጋዜጠኝነት የህዝብ ሃብት ሆነው እንዲቀጥሉ የጋዜጠኞችን መብት ማስከበር እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

የሚዲያ ባለሙያ ሙያዊ ስነ ምግባርን ባከበረ መልኩ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ማድረግ ደግሞ የሁሉም ኃላፊነት ነው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ ግዛው ተስፋዬ፣ ዜጎችን የመረጃ ተደራሽ ለማድረግ ባለፉት ዓመታት በርካታ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡

ለአብነትም መገናኛ ብዙሃንን ለማስፋፋት፣ ተደራሽነታቸውን ለማረጋገጥ እንዲሁም ልዩ ልዩ ድጋፍና ማበረታቻዎችን በማድረግ አቅማቸው ለመገንባት የሚያሥችሉ የፖሊሲ እና የህግ ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም በዲጂታል ሚዲያ የሚንቀሳቀሱ የመገናኛ ብዘሃን ተቋማት እውቅና የሚያገኙበት አሰራር መዘርጋቱንም ጠቁመዋል፡፡  

በመርሃ ግብሩ የተሳተፉ ጋዜጠኞችም የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ለህብረተሰቡ ትክክለኛ መረጃ ለማድረስ  መትጋት አለባቸው ብለዋል፡፡

ማህበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም የራሳቸውን የግል ዓላማ የሚያራምዱ አካላት በህግ አግባብ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ሊገነዘቡ እንደሚገባም ነው የተናገሩት፡፡  

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም