የብልጽግና ፓርቲ አንደኛ ጉባኤ የቅድመ ጉባኤ መድረክ ተጠናቀቀ

62

መጋቢት 01 ቀን 2014 (ኢዜአ) ለሶስት ቀናት በአዳማ ከተማ ሲያካሂደው የነበረው የብልጽግና ፓርቲ አንደኛ ጉባዔ የቅድመ ጉባኤ መድረክ በዛሬው ዕለት ተጠናቋል፡፡

በማጠቃለያ መድረኩ ተገኝተው ማብራሪያ የሰጡት የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ደመቀ መኮንን ከዚህ ቀደም በሀገራችን የሰራነውን የማፍረስ፣ አንድ ከሚያደርጉን ይልቅ በሚያለያዩን ጉዳዮች ላይ ትኩረት ተደርቶ መስራት እንዲሁም ገቢራዊነት መጓደልና ግለሰቦች ከሀገር በላይ የሆኑበት ሁኔታዎች ይስተዋሉ ነበር ብለዋል፡፡

ብልጽግና ፓርቲ እነዚህን ችግሮች በሚፈታ መልኩ እየተጓዘ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡

ባለፉት ሶስት ዓመታት በበርካታ ተግዳሮቶች ውስጥም ሆነን የሀገራችንን ሉዓላዊነት በማስጠበቅ ስኬቶችን አስመዝገበናል ያሉት አቶ ደመቀ መኮንን፤ ፈተናውን በዘላቂነት ለመሻገርና ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ አንድነትን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

የፓርቲው አመራርና አባላት በጥብቅ ዲሲፕሊን መመራት እንዳለባቸውም ገልፀዋል፡፡

በትስስርና እውቅና መስራት ብሎም ብልሹ አሰራሮች ለፓርቲው ጠንቅ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ተግባሮችን ስንፈጽም በፓርቲው ህግና ደንብ እንዲሁም እሴቶችና መርሆዎች ተገዝተን መሆን አለበት ብለዋል፡፡

ፓርቲው በቀጣይም ጥራት ላይ የተመሠረተ የአባላት ብዛት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አስታውቀዋል፡፡

የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አደም ፋራህ በበኩላቸው ከስርዓትና ከተልዕኮ አፈፃፀም ጋር የሚያያዙ ችግሮችን መፍትሄ በመስጠት እንዲሁም ውስጣዊ አንድነትን በማጠናከር የፓርቲውን የአጭር ጊዜ እቅዶችና የረጅም ጊዜ ራዕይ ማሳካት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

አመራሩና መላ አባላቱ ጽንፈኛ ብሔርተኝነትን አምርረው እንዲታገሉ ማሳሰባቸውን ከፓርቲው የማህበራዊ ትስስር ገጽ የተገኘው መረጃ አመልክቷል።

ኢትዮጵያን እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ‼

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም