አደዋ ለብልፅግና ማማ….‼

139

በቀደሰ ተክሌ (ሚዛን ኢዜአ)  

ዓድዋ ከቦታ ስያሜነት ያለፈ ትርጉም ያለው ዓለም አቀፍ የነፃነት መገለጫ ሆኖ በክብር ይጠራል። ከድልም በላይ ድል የራስ የማንነት ክብርን ያስጠበቀ ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካውያን የቅኝ ግዛት ቀንበር እንዲለዝብ ብሎም እንዲወገድ ያስቻለ ዝንተ ዓለም ሲከበር የሚኖር የታሪክ ክስተት ነው።

ለዓለም ነፃነትን ያበረከተች የምድረ ኢትዮጵያ አንዷ ከፍልም ነች አድዋ!። አድዋ ጣሊያንን ሽንፈት በማከናነብ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ከማስከበር ከፍ ብሎ አድማስ በመሻገር ዓለም ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ መፍጠር የቻለ የድል ቦታ፣ የድል አድራጊነትና የጀግንነት አርማ።

ያኔ ዓድዋ እውነቱን ገሃድ እስክታወጣ ድረስ ነጮች አሸናፊዎች፣ ገዥዎች እና የፈለጉትን ማድረግ የሚችሉ። ጥቁሮች ደግሞ የበታችና ለባርነት የተፈጠሩ አድርገው በመሳል የንቀታቸውን ጥግ አሳይተዋል።

አፍሪካን ተቀራምተው ሀብቷን ንብረቷን የኢኮኖሚያቸው ማሳደጊያ ህዝቦቿን ደግሞ ማጓጓዣ አድርገው እየተጠቀሙ ባሉበት ወቅት እግር ጥሏቸው፤ እድል ገጥሟቸው ጣሊያናውያን በቅኝ ግዛት እሳቤ የኢትዮጵያን ምድር ረገጡ። ግና እንደሌላው በጀ ብሎ የባርነት ቀንበር በጫንቃው የሚሸከም ኢትዮጵያዊ ታጣ፤ ይህም ራስ ምታት ሆኖባቸው ቆየ፤ ጥቁር ህዝቦች የበላይነት ተቆናጠው ዓለም እጁን በአፉ ጫነ።

ዓድዋ የድል ተራራ እንድትሆን ያደረጓት ኢትዮጵያውያን ስለ ሥጋቸውና ነፍሳቸው እንኳ ግድ ሳይሰጡ ኢትዮጵያን ብቻ ብለው በመውጣታቸው ነው ለድል የበቁት። በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ትምህርት ክፍል መምህር አጥናፉ ምትኩ እንደሚሉት ኢትዮጵያ በዓድዋ ጣሊያንን የማሸነፏ ሚስጥር ህዝቦቿ የንጉሱን ጥሪ ተቀብለው በአንድነት መውጣታቸው ነው። አንድነት የወለደው ጀግንነት ከወኔና አልበገር ባይ ስሜት ጋር ተሳስረው አውሮፓዊቷን  ኃያል  ሀገር  መጣል  የቻሉበት ደማቅ ታሪክ ነው ይላሉ።

በዓድዋ ኢትዮጵያ ቅኝ አገዛዝን በመቃወም ሰዎች ሁሉ እኩል መሆናቸውን ያበሰረች ሲሆን፤ ይህም ለአፍሪካውያን የነፃነት ጮራ ፈንጣቂ አድርጓታል። ድል አድራጊነትን በአፍሪካ ምድር አሐዱ ብላለች ኢትዮጵያ። 

ጥቁር እና ነጭ የቆዳ ቀለም እንጂ የበላይና የበታች መገለጫ አለመሆኑን በተግባር አረጋግጣለች፤ ለዓለም ሕዝቦች ይህንኑ አሳይታለች። ሀገራችን ነጮች በጥቁሮች ላይ የያዙት የነበረውን የበታችነት እሳቤ በጀግኖች ልጆቿ የተባበረ ክንድ ድል በማድረግ በጀግንነት ጭምር ማሳየቷን ነው ምሁሩ የሚናገሩት።

በዓድዋ ጦርነት ኢትዮጵያ ድል መቀዳጀቷ ተከትሎ በዓለም ላይ ብዙ ተጽዕኖዎች መፈጠራቸውን ጠቅሰው ለአብነትም አፍሪካን ተቀራምተው እንደፈለጉ ሲያደርጉ የነበሩ ነጮች ስጋት ውሰጥ መግባታቸውን አንስተዋል።

ጥቁር አፍሪካውያን እንዲህ ማድረግ ይችላሉ ወይ ? የሚል ጥያቄን በውስጣቸው በማመላለስ ስለ አፍሪካውያን ማንነት እንዲያጤኑ አስገድዷል፣ እድልም ፈጥሯል። ይህ ደግሞ በጥቁሮች ላይ የነበራቸውን ያልተገባ የበታችነት ትርክት ሳይወዱ በግድ እንዲቀይሩ አድርጓል ሲሉ አብራርተዋል።

አፍሪካ አውሮፓን የሚገዳደር ጦር እንዳላት ያሳየው የዓድዋ ድል በተለይ ኢትዮጵያን የነፃነት ቀንዲልነትን አጎናጽፏታል ብለዋል። በራስ መተማመንና ራስን መቻል መንፈስ በወኔ ከመሙላት ባለፈ የኢትዮጵያ አንድነት በማጠናከር ሉዓላዊነቷ ያልተደፈረና የተከበረች ሀገር እንድትሆንአስችሏል።

ይህም ደግሞ አፍሪካውያን ለነፃነታቸው እንዲታገሉ በር ከፍቷል፣ ለፓንአፍሪካኒዝም ንቅናቄ መፈርጠም ጉልበትና ኃይል ሆኗል፤ሲሉ መምህር አጥናፉ ያስረዳሉ።

የዓድዋ የድል ጮራ በዘመን የሚሻር በታሪክ ብቻ ተነግሮ የሚተው አይደለም የሚሉት ደግሞ ሌላኛው የታሪክ መምህር ዓለማየሁ አብርሃም ናቸው። እሳቸው እንዳሉት ትናንት ሀገራችንን ለማንበርከክ የዳዱ እጆች ዛሬም በእጅ አዙር ሊያዳክሙን እየተውተረተሩ ነው።

የዓድዋ ጀግንነት ገድል ለጦርነት ብቻ ሳይሆን ለልማታችንም ልናውለው እንደሚገባ የሚናገሩት መምህር ዓለማየሁ የትናንቱን የ"እችላለሁ" ባይነት ወኔ እና የመንፈስ ጥንካሬ ዛሬም የማይደፈር የሚመስለውን በመድፈር ይህ ትውልድ አኩሪ ታሪክ  የሰራበት ታላቅ ተግባርአከናውኗል።

የኢትዮጵያውያን  የተባበረ ክንድ የሚሳነው ነገር እንደሌለ ታሪክን በመድገም አረጋግጧል።

ወርሃ የካቲት ያኔ ነፃነትን ስታቀዳጀን ዛሬ ደግሞ ብርሃን እንካችሁ ያለች ቅድስት ነች ብለዋታል።ሁለቱንም ድሎች የሚያመሳስላቸው ህብረት፣ በአንድነት መሰለፍና ለአንድ ዓላማ የመረባረብ ውጤት መሆናቸውን ነው ያስረዱት። 

ኢትዮጵያ ያለ ዘመናዊ ጦር መሳሪያ ጣሊያንን ድል አድርጋለች።  ዛሬም ልጆቿን አስተባብራ  ታሪክ እየሰራች ነው። ይህ ታዲያ የማሸነፍ ሞራል በትውልድ ቅብብሎሽ  ለዛሬ መድረሱንና ለነገም የሚቀጥል ስለመሆኑ ማሳያ ነው ይላሉ መምህር ዓለማየሁ።

ለሀገራችን በጎ የማያስቡናየማይመኙይህንየኢትዮጵያውያን የአይበገሬነት መንፈስ  ለመሸርሸር ዛሬም እንደትላንቱ ሉዓላዊነቷን ለመድፈር ቢሞክሩም  ለዚህ በጀ የሚል ኢትዮጵያዊ ግን ማግኘት አልቻሉም። በዘር፣ በሃይማኖትና  ጎሳ  ከፋፍለው ትንሽ ህዝብ በማድረግ እንደፈለጉ ለመግዛት  ቢጥሩም ቅሉ የአንድነታችን ሚስጢር የደም ዋጋ በአባቶቻችን የተከፈለበት ነውና አይችሉንም፣መቼም አይሳካላቸውም ሲሉ አስምረውበታል።

ነገ ሌላ ብዙ ዓድዋ ይጠብቀናል፤ ለዚህ  የዓድዋ  ድል መብቃት የሚችል ትውልድ መቅረጽ የሚቻለው አሁን ነው። በመናገር  ብቻ ሳይሆን  ትውልድ ተሻጋሪ ታሪክ በመስራት ለልጆቻችን ዓድዋን እናስተምር። 

በመከፋፈል ሳይሆንአንድ  በመሆን ስለ አንዲት ኢትዮጵያ በመቆም ዓድዋን ህያው እናድርግ። የጥላቻን ትርክት ፍቀን በማስወገድ፣ ትክክለኛ  ዓድዋን በፍቅር ብዕር ብራና ላይ ከትበን እናስቀምጥ። ያኔ ኢትዮጵያ የብዙ ዓድዋ ባለቤት ትሆናለች። ከብዙ ዓድዋ የሚገኝ ድል ደግሞ ለብልፅግና  ማማ መሰላል ይሆናል እንላለን።ቸር እንሰንብት ሠላም ….‼።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም