አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ለውጥ አስመዝግቧል

107

የካቲት 15 ቀን 2014 (ኢዜአ) አገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው በፈተና ውስጥም ቢሆን ለውጥ ማስመዝገቡን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ተናገሩ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ ነው፡፡

በዚህም ባለፉት ሶስት ዓመታት የተደረገው የገንዘብ ለውጥ፣ የፋይናንስ ዘርፍ ማሻሻያዎች እንዲሁም የካፒታል ገበያ መቋቋሙ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ 

ከዚህ ቀደም የተጀመሩና የተጓተቱ የፕሮጀክት አፈጻጸሞችን ለማስተካከል የተወሰዱ አዳዲስ የአሰራር ማሻሻያዎች ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ሌሎች ፕሮጀክቶች ገጥሟቸው የነበሩ ችግሮችን በመቅረፍ ረገድ ከፍተኛ ሚና መጫወታቸውን አውስተዋል፡፡

ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 200 ሺህ አዳዲስ የንግድ ፈቃድ መሰጠቱንና 845 ሺህ የንግድ ፈቃድ መታደሱንም ነው የጠቀሱት፡፡

በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ ከተገነቡት 177 ሼዶች መካከል 158ቱ ለባለሃብቶች መተላለፋቸውንና ከእነዚህ ውስጥ 104ቱ ሙሉ በሙሉ ስራ መጀመራቸውንም አስረድተዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ደረጃ በተከሰተው የሸቀጦች ዋጋ ጭማሪ ምክንያት ከፍተኛ የዋጋ ግሽበት መመዝገቡን ገልጸው፤ ግሽበቱ አሁንም ፈተና ሆኖ መቀጠሉን ተናግረዋል፡፡

ኢትዮጵያን እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ‼

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም