የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት መልካም ዜና ነው

89

አዲስ አበባ፣ የካቲት 09/2014 (ኢዜአ) የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት መልካም ዜና መሆኑን በዘርፉ ስራ ላይ የተሰማራው የሰሜን ኢኮቱርስ መስራችና ባለቤት ማርኮ ዳጋስፐር ተናገረ።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ትናንት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ "የአገር ህልውና እና ሉዓላዊነት ላይ የተደቀነን አደጋ ለመከላከል” ተግባራዊ ሲደረግ የቆየውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ  ማንሳቱ ይታወሳል።

ለአዋጁ መነሳት በምክንያትነት ከተጠቀሱት ጉዳዮች መካከል በኢንቨስትመንት፣ ቱሪዝም ፍሰትና ዲፕሎማሲያዊ አንድምታው አሉታዊ ተፅእኖ ስላለው ነው።

ከዓመታት በፊት ኢትዮጵያን ለመጎብኘት የመጣው ጣሊያናዊው ማርኮ ዳጋስፐር፤ ‘ሰሜን ኢኮቱርስ’ የተሰኘ የቱሪስት ድርጅት በማቋቋም በኢትዮጵያ ቱሪዝም ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል።

ምድረ ቀደምቷ ኢትዮጵያ በባህላዊና ተፈጥራዊ ሀብቶች የታደለች በመሆኗ በቱሪዝም ፍሰቱ ትልቅ አቅም ያላት አገር መሆኗን ደጋግሞ ይናገራል።

በመሆኑም ላለፉት ሶሰት ወራት ሲተገበር የቆየው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለቱሪስት እንቅስቃሴው አሉታዊ ተፅእኖ እንደነበረው ይታመናል።

አሁን ላይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳቱ ግን ለቱሪዝም ፍሰትና ነፃ እንቅስቃሴ ወሳኝ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ማርኮ ዳጋስፐር ይናገራል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ በርካታ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በተለያዩ አገራት የጉዞ ማስጠንቀቂያ የወጣባችው እንደነበሩ አስታውሶ የአዋጁ መነሳት ለቱሪዝም ዘርፍ መልካም ዜና ነው ብሏል።

ለስድስት ወራት እንዲቆይ የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳቱ ነፃ የጉዞ እንቅስቃሴ እንዲኖርና በተለይም የቱሪስቶችን ፍሰት የሚያጠናክር መሆኑን ገልጿል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም