ባህላዊ ስፖርቶችን ለዘላቂ ሰላምና ልማት መጠቀም ይገባል-ሚኒስቴሩ

129

ደብረብርሀን ፤ የካቲት 6 ቀን 2014 (ኢዜአ)ትውልዱ ባህላዊ ስፖርቶችን ለዘላቂ ሰላምና ልማት ሊጠቀምባቸው እንደሚገባ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አስገነዘበ ።

19ኛው የሀገር አቀፍ የባህል ስፖርት ውድድርና 15ኛው የባህል ፌስቲቫል ዛሬ በደብረብርሀን ከተማ ተጀምሯል።

ውድድርና ፌስቲቫሉ ከየካቲት 6 እስከ 13 ድረስ  የሚካሄድ መሆኑ ተመላክቷል።

የባህልና ስፖርት ሚኒስትር አቶ ቀጀላ መርዳሳ  ውድድርና ፌስቲቫሉን ባስጀመሩበት ወቅት እንደገለጹት ባህላዊ ስፖርት በኢትዮጵያ  ህዝቦች መካከል  ልዩ ትርጉም አለው ።

"ባህላዊ እሴቶቻችንን ማጎልበት ጠንካራ አገራዊ አንድነታችን  ለማሳደግ  የሚጠቅም በመሆኑ ወጣቶች ከአባቶቻቸው የተረከቡትን የባህል አደራ  ሊጠብቁና ሊንከባከቡ ይገባል" ብለዋል ።

"የባህል ስፖርት  ለአካል ብቃት ጥንካሬና  ለአእምሮ እድገት  ከሚሰጠው ፋይዳ  በላይ የማህበረሰብ   ማንነት የሚገለጥበት ሀብት ነው ዕ ሲሉም አክለዋል ።

"የኢትዮጵያን የባህል ስፖርት በዓለም አቀፍ ደረጃ  በተባበሩት መንግስታትየትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም (በዩኒስኮ ) እንዲመዘገብ ሚኒስቴሩ ከባህል ስፖርት ፌደሬሽን ጋር  በጋራ ይሰራል" ብለዋል ።

የአማራ ክልል ባህልና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ አማኑኤል ፈረደ በበኩላቸው   በክልሉ በኮሮና ወረርሽኝ እና በህውሓት ወራራ   ምክንያት የስፖርት እንቅስቃሴዎች ተቋርጠው  መቆየቱን ተናግረዋል ።

የሽብር ቡድኑ  በፈጸመው ወረራ በወልድያ ዓለም አቀፍ ስቴድየም 160 ሚሊየን ብር የሚገመት ሀብት ማውደሙን ገልጸው ዘርፉን  ወደቀደመው  እንቅስቃሴ  ለማስገባት መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት ድጋፍ እንደሚያስፈል አስታውቀዋል ።

በደብረብርሀን ከተማ ዛሬ የተጀመረው የባህል ስፖርት ውድድር  በ10 ባህላዊ የስፖርት ዓይነት የሚካሄድ መሆኑን አስታውቀዋል   ።

በውድድሩ የአማራ፣  የአፋር፣  የደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ሀዝቦች፣  የደቡብ፣  የሲዳማ፣ የኦሮሚያ፣  የቤሻንጉል ጉሙዝ ክልሎችና የአደስ አባባና የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር ተሳታፊ ሆነዋል ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም