43ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ ተጀመረ

81

ጥር 12 ቀን 2014 (ኢዜአ) 43ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብስባ ዛሬ ተጀመረ።

ስብሰባው “የአፍሪካ አህጉርን የስርዓተ ምግብ አቅም መገንባት፣ የሰው ሃብት ልማት፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማትን ማፋጠን” በሚል የአፍሪካ ሕብረት ባዘጋጀው የ2022 መሪ ቃል የሚካሄድ ነው።

በበይነ መረብ እየተካሄደ ባለው ስብሰባ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳ ፋቂ ማህማት፣የኮሚቴው ሰብሳቢ እና የሕብረቱ አባል አገራት አምባሳደሮች እየተሳተፉ ነው።

ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆየው ስብሰባ ጥር 25 እና 26 ቀን 2014 ዓ.ም ለሚካሄደው 40ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብስባ እንዲሁም ጥር 28 እና 29 ቀን 2014 ዓ.ም ለሚከናወነው 35ኛው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚቀርቡ ረቂቅ አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል።

በተጨማሪም ኮሚቴው በአፍሪካ ሕብረት ስር የሚገኙ የተለያዩ ተቋማት የአፈጻጸም እንዲሁም ሕብረቱ እ.አ.አ በ2021 ያካሄዳቸውን ስብስባዎች የተመለከቱ ሪፖርቶችን ያደምጣል።

40ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤትና 35ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ በኢትዮጵያ እንዲካሄድ መወሰኑ ይታወቃል።

ኢትዮጵያን እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ

‼

ሀገርን በዘላቂነት እናልማ

‼

የፈረሰውን አብልጠን እንገንባ

‼

ለማንኛውም ፈተና እንዘጋጅ

‼
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም