አሸባሪው የህወሃት ቡድን ሰላማዊ ዜጎችን በመጨፍጨፍና የህዝብ ሃብትን በማውደም ኢትዮጵያን ጠልነቱን በተግባር አሳይቷል

70

ታህሳስ 12/2014/ኢዜአ/ አሸባሪው የህወሃት ቡድን ሰላማዊ ዜጎችን በመጨፍጨፍና የህዝብ ሃብትን በማውደም ኢትዮጵያን ጠልነቱን በተግባር ማሳየቱን በሰሜን ወሎ ዞን የድሬ ሮቃ ቀበሌ አስተዳዳሪ ሃሰን ከረሙ ገለጹ፡፡

የሽብር ቡድኑ በወገን ጥምር ጦር ተሸንፎ ከድሬ ሮቃ ፈርጥጦ በመወጣበት ወቅት የአፋር፣ የአማራና ትግራይ ክልሎችን የሚያገናኘውን ዋና መስመር ላይ ከፍተኛ ጉዳት አድርሷል፡፡

የሽብር ቡድኑ በድሬ ሮቃ ቀበሌ በጨረቲ ወንዝ የተገነባውን ግዙፍ መተላለፊያ ድልድልይን ሰብሮ ከጥቅም ውጭ አድርጎታል።

የአካባቢው ሰዎች "አርሶ አደሩ ጀኔራል" ሲሉ የሚጠሯቸው የድሬሮቃ ቀበሌ አስተዳዳሪ ሀሰን ከረሙ የሽብር ቡድኑ ወራሪ ኃይል በአካባቢው በሚኖሩ ዜጎች ላይ ከፍተኛ ግፍ መፈጸሙን ተናግረዋል፡፡

ከግለሰብ ቤት እስከ ህዝብ ሃብት ድረስ ዘረፋና ውድመት መፈጸሙን ጠቅሰው፤ በዚህም ቡድኑ ኢትዮጵያ ጠል መሆኑን በተግባር ማሳየቱን ነው ያብራሩት፡፡

የሽብር ቡድኑ ወራሪ ኃይሎች የገበሬውን እንስሳት ጭምር አርደው መብላታቸውንና መዝረፋቸውን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የአሸባሪ ቡድኑ ዋነኛ ዓላማ በሁሉም አካባቢ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን በመግደልና በመዝረፍ አንገት ማስደፋት መሆኑን ገልጸው፤ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች የሽብር ቡድኑን ቅዠት ከንቱ ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

የሀገር መከላከያ ሠራዊቱ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ያደረገውን ተጋድሎም አድንቀዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም