ለወልዲያ ከተማና አካባቢው አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው ተንቀሳቃሽ ማከፋፈያ ጣቢያ በአሸባሪው ህወሓት ተነቅሎ ተወስዷል

205

ታህሳስ 11/2014 (ኢዜአ) ዶሮ ግብር በተባለው ቦታ ለወልዲያ ከተማና አካባቢው አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው ባለ 230/33/15 ኪሎ ቮልት ተንቀሳቃሽ ማከፋፈያ ጣቢያ በአሸባሪው ቡድን ተነቅሎ መወሰዱን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ።

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የባለሙያዎች ቡድን በስፍራው ተገኝቶ እንዳረጋገጠው ተንቀሳቃሽ ማከፋፈያ በአሸባሪው የህወኃት ቡድን ተነቃቅሎ ተወስዷል።

ማከፋፈያ ጣቢያው ከወልዲያ ነባር ባለ 66 ኪሎ ቮልት ማከፋፈያ ጣቢያ ጋር በመሆን ለወልዲያ ከተማ፣ ለወልዲያ ዪኒቨርሲቲ፣ ጭፍራ፣ ሲሪንቃ፣ ሳንቃ፣ ኡርጌሳ፣ ውጫሌ፣ ጉባላፍቶ፣ ቃሊም፣ ጉብዬ፣ ሀራ፣ ሮቢት ቆቦ ጊራና ከተሞችና አካባቢያቸው የሚሄዱ መስመሮች ነበሩት።

የሽብር ቡድኑ ተንቀሳቃሽ ማከፋፈያ ጣቢያውን ጨምሮ ከነባሩ የወልዲያ ማከፋፈያ ጣቢያ የሥርጭት ትራንስፎርመሮችን ነቅሎ መውሰዱንና የትራንስፎርመር ዘይት ገልብጦ መውሰዱን ማረጋገጥ ተችሏል።

የሽብርተኛው የህወኃት የዘረፋ ቡድን ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች የተዋቀረና ትራንስፎርመሩ ችግር አለበት ወይስ የለውም የሚለው እየተፈተሸ መወሰዱንም ነው የተገለጸው።

በባለሙያዎች ቡድኑ የሚቀርበውን መነሻ መሰረት አድርጎ የጥገና ቡድኑ ከነሐሴ 2 ቀን 2013 ዓ/ም ጀምሮ የተቋረጠውን የወልዲያና አካባቢው ኤሌክትሪክ ለማገናኘት በፍጥነት የጥገና ሥራውን እንደሚጀምር የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም