ፖላንድ የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ እደግፋለሁ አለች

85

ህዳር 30 ቀን 2014 (ኢዜአ) ፖላንድ የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳን በተመረጡ ዘርፎች ላይ ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኗን አረጋገጠች።

16ኛው የኢንተርኔት አስተዳደር ፎረም በፖላንድ እስተናጋጅነት እየተካሄደ ነው። ከፎረሙ ጎን ለጎን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ ከፖላንድ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የዲጂታል ፖሊሲ አማካሪ ሚኒስትር ክሪሺሽቶቭ ሹበርት ጋር ተወያይተዋል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ ኢትየጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂ ቀርፃ በግብርና፣ ቱሪዝም፣ አምራች ኢንደስትሪና በአይሲቲ ዘርፍ አስቻይ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እየሰራች መሆኑን አብራርተዋል።

ኢትዮጵያ በእነዚህና በሌሎችም የዲጂታል ልማት መስኮች ዙሪያ በትብብር መስራት እንደምትፈልግም ገለፀዋል።

የፖላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር የዲጂታል ፖሊሲ አማካሪ ሚኒስትር ክሪሺሽቶቭ ሹበርት በበኩላቸው ሀገራቸው በዲጂታል ልማት ዙሪያ ያላትን ልምድ ለሚኒስትር ዴኤታዋ አጋርተዋል፡፡

የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳን በተመረጡ ዘርፎች ላይ ለመደገፍ ፖላንድ ቁርጠኛ መሆኗንም ማረጋገጣቸው ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም