የመዲናዋ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በገላን ከተማ መሪን ቀበሌ የዘማቾችን ሰብል ሰበሰቡ

80

ህዳር 29/2014(ኢዜአ) የአዲስ አበባ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በገላን ከተማ መሪን ቀበሌ የሚገኝ የዘማቾች ቤተሰቦች ሰብል ሰብስበዋል።
የሰብል መሰብሰቡን ስራ ያስተባበረው የአዲስ አበባ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና የበጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ነው።

አሸባሪው ህወሓት በአገር ሕልውና ላይ ደቅኖት የነበረውን አደጋ ለመቀልበስ መንግስት ባደረገው ጥሪ በርካታ ዜጎች ሠራዊቱን ተቀላቅለዋል።

በመሆኑም የእነዚህን ዘማቾች ቤተሰቦች ለማገዝና ለማበረታታት የተለያዩ ሥራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ።

ከዚህም ውስጥ ሰብል መሰብሰብ አንደኛው ሲሆን ዛሬ 200 የሚጠጉ በጎ ፈቃደኞች በዚሁ ሥራ ተሳትፈዋል።

የኮሚሽኑ በጎ ፈቃድ ዳይሬክተር ዳዊት ሙሉጌታ በግንባር ለሚገኘው ሠራዊት ከሚደረገው ድጋፍ ባሻገርመስዋዕትነት   እየከፈሉ  የሚገኙ ዘማቾች ቤተሰቦችንም በምንችለው ሁሉ መደገፍ አለብን ብለዋል።

በሰብል ስብሰባው የተሳተፉ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በበኩላቸው፤ ዘማቾች ሕይወታቸውን መስዋዕት በማድረግ የአገር ሕልውና ለማስጠበቅ ተሰማርተዋል፤ እኛ ደግሞ የዘሩትን ሰብል በመሰብሰብ ደጀንነታችንን ማሳየት ይገባናል ብለዋል።

በቀጣይም ለዘማች ቤተሰቦች ተመሳሳይ ድጋፎችን እንደሚያደርጉ ገልጸዋል።

ወጣት አለማየሁ አያሌውናወልጌኛ ሁንዴሳ የዘማቹን ቤተሰብ ማገዝ እኛን ለመጠበቅ ደሙን አፍስሶ አጥንቱን ከስክሶ አገር ሊያቆና ለሄደ ወታደር የእሱን ቤተሰብ  መደገፍ አለብን ብለዋል።

የገላን ከተማ ከንቲባ ወይንሸት ግዛው በበኩላቸው፤ በከተማዋ የሚገኙ የዘማች ቤተሰቦችን የመደገፉ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።

ኅብረተሰቡ እርስ በእርሱ በመተጋገዝ፣ በንቅናቄ የዘማች ቤተሰቦችን የመደገፍ፣ ለሠራዊቱ በአይነትና በገንዘብ የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ እየተሳተፈ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም