ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጠላት ኃይል እጁን እንዲሰጥ ያቀረቡትን ጥሪ ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች እጃቸውን እየሰጡ ነው

71

ህዳር 25 ቀን 2014 (ኢዜአ) ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የጠላት ኃይል እጁን እንዲሰጥ ያቀረቡትን ጥሪ ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ የአሸባሪው ሕወሓት ታጣቂዎች እጃቸውን እየሰጡ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወደ ግንባር አምርተው የወገንን ጦር መምራት ከጀመሩበት ጊዜ ጀምሮ በሁሉም ግንባር ድል እየተመዘገበና የጠላት ሀይል እየተበታተነ ነው።

'በዘመቻ ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት' የወገን ጦር ድል በድል እየደራረበ ሲገሰግስ በአንፃሩ የጠላት ኃይል በየጦር ግንባሩ ሽንፈትን እየደረሰበትና እየተደመሰሰ ይገኛል።

ለአብነትም በጋሸና፣ በሸዋ፣ በወረኢሉ፣ በጭፍራ እና በሌሎች ግንባሮች የወገን ጥምር ጦር ባደረገው ተጋድሎ በርካታ ከተሞችን ከወራሪው ኃይል ነፃ ማድረግ ችሏል፣ የወራሪው ቡድንም ከፍተኛ ሰብዓዊና ቁሳዊ ኪሳራ ደርሶበት በመፈርጠጥ ላይ ይገኛል።

ከመደምሰስ የተረፈው የወራሪና ዘራፊ ቡድኑ ኃይልም እየተበታተነ ሲሆን የወገን ጦር በየግንባሩ የተበታተነውን የጠላት ኃይል የመልቀም ስራዎችን አጠናክሮ ቀጥሏል።

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ራዕይና ግቡ በማይታወቅ ጦርነት በዕውር ድንብር ጁንታው ያሰለፋቸው የትግራይ ወጣቶች እንደ ቅጠል እየረገፉ መሆኑን መግለፃቸው አይዘነጋም።

በዚህም ወጣቶች በማያውቁት አካባቢና ራዕይ በሌለለው ጦርነት ገብተው እንዳያልቁ እጃቸውን ለመከላከያ ሰራዊትና ለክልል የፀጥታ ኃይሎች እንዲሰጡ ጥሪ ማቅረባቸው ይታወሳል።

የትግራይ እናቶችም ልጆቻቸው ራዕይ በሌለው ጦርነት እንዳያልቁ "ልጆቻችን የት ደረሱ" ብለው መጠየቅ እንዳለባቸው መግለፃቸው አይዘነጋም።

የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ ተከትሎም በሺዎች የሚቆጠሩ የሽብር ቡድኑ ለውጊያ ያሰለፋቸው ታጣቂዎች እጃቸውን ለወገን ኃይል እየሰጡ ነው።

እጃቸውን የሰጡት ምርኮኞቹም ባለማወቅና በመገደድ ወደ ውጊያ መሰለፋቸውን ገልፀው፤ ቡድኑ በደረሰበት ሽንፈት እጅ ለመስጠት መገደዳቸውን ገልፀዋል።

የሽብር ቡድኑ አባላት ከተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች በቤተሰብ ልጅ አምጡ እየተባሉ በአሸባሪው ተገደው ቢሰለፉም በእስካሁኑ ድርጊታቸው ተፀፅተው ይቅርታ ጠይቀዋል።

አሸባሪው ቡድን የሚያሰራጨው መረጃ ሀሰተኛ መሆኑን መሬት ላይ ያለው እውነታ ግን አሸባሪ ቡድኑ ተሸንፏል ብለዋል።

በርካታ ጓደኞቻቸው በከንቱ ሕይወታቸውን የሚናገሩት ምርኮኞቹ፤ እነርሱ ግን እጃቸውን ለመከላከያ በመስጠታቸው እድለኞች ነን ብለዋል።

እጅ ከሰጡበት ጊዜ ጀምሮ በመከላከያ ሰራዊትና በህብረተሰቡ ለተደረገላቸው እንክብካቤ  አመስግነዋል።

ሌሎች የትግራይ ወጣቶችም በአሸባሪው ቡድን እያሸነፍን ነው በሚል በሚዲያ በሚነዛው ሀሰተኛ መረጃ እየተደናገሩ ለውጊያ እንይሰለፉ፣ ውጊያ ላይ የተሰለፉትም እጃቸውን እንዲሰጡ ጥሪ አቅርበዋል።

የትግራይ ወጣቶች በጁንታው ጦርነት ከመማገድ ይልቅ ለወገን ጦር እጃቸውን በመስጠት ሕይወታቸውን ማዳን እንዲችሉ የኃይማኖት አባቶች ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም ጥሪ ቀርቧል።

በየግንባሩ ተሸንፎ የተበታተነው የጠላት ኃይል የዘረፈውን ሀብት ይዞ እንዳይሸሽ ህብረተሰቡ አካባቢውን ተደራጅቶ እንዲጠብቅ፣ ብሎም የወራሪው ኃይል አባላትን እየማረከ ለመከላከያ ሰራዊት እንዲያስረክብ መንግስት ጥሪ ማቅረቡ ይታወሳል።

_ አካባቢህን ጠብቅ፣

_ ወደ ግንባር ዝመት፣

_ መከላከያን ደግፍ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም