የኢትዮ-ካናዳውያን ኔትወርክ ለማህበራዊ ድጋፍ በአፋር ክልል ለተፈናቀሉ ዜጎች 50 ሺህ የካናዳ ዶላር ድጋፍ አደረገ

63

ህዳር 11 ቀን 2014 (ኢዜአ) የኢትዮ-ካናዳውያን ኔትወርክ ለማህበራዊ ድጋፍ በጦርነት ምክንያት በአፋር ክልል ለተፈናቀሉ ዜጎች 50 ሺህ የካናዳ ዶላር ድጋፍ ማድረጉን አስታወቀ።

ባለፈው ሁለት ሳምንት ውስጥ ለሰብአዊ ድጋፍ የሚውል ከ175 ሺህ የካናዳ ዶላር በላይ ማሰባሰቡንም ገልጿል። 

የኢትዮ-ካናዳውያን ኔትወርክ ለማህበራዊ ድጋፍ በጦርነቱ ምክንያት በአፋር ክልል ለተፈናቀሉ ዜጎች 50 ሺህ የካናዳ ዶላር በአፋር ልማት ማህበር በኩል መስጠቱን ለኢዜአ በላከው መግለጫ አስታውቋል።

36 ሺህ 302 ነጥብ 5 የካናዳ ዶላር ከሃሊፋክስ ከተማ ነዋሪዎች እንዲሁም 11 ሺህ 334 የካናዳ ዶላር ኤድመንተን ከሚገኙ ነዋሪዎች የተሰበሰበ ሲሆን፤ የተቀረው 2 ሺህ 363 ነጥብ 5 ዶላር ከድርጅቱ የአስቸኳይ እርዳታ አካውንት የተገኘ መሆኑን አመልክቷል።

"ለአስቸኳይ የእናት አገር ጥሪ ምላሽ" በሚል ድርጅቱ በጦርነቱ ለተፈናቀሉ ዜጎች ጥቅምት 28 ቀን 2014 ዓ.ም ካካሄደው የበይነ መረብ መርሃ ግብር አንስቶ እስካሁን ከ175 ሺህ የካናዳ ዶላር በላይ ማሰባሰቡንና አሁንም ድጋፉ እንደቀጠለ ገልጿል።

በቀጣይ ለሰብአዊ ድጋፍ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር በኦቶዋና ቶርንቶ ከተሞች እንደሚያካሄድ ጠቁሟል።

ድርጅቱ ከተቋቋመበት ሕዳር ወር 2013 ዓ.ም አንስቶ እስካሁን ለወቅታዊ አገራዊ ጥሪና ለልማት ፕሮጀክቶች  ከ148 ሚሊዮን ብር በላይ አሰባስቦ መርዳቱንም አመልክቷል።

ድጋፍ ከተደረገው ገንዘብ ውስጥ ከ15 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ የተሰጠ መሆኑን አስታውቋል።

ለሕልውና ዘመቻውና ለልማት ስራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጉን እንደሚቀጥልም አስታውቋል።

_ አካባቢህን ጠብቅ፣

_ ወደ ግንባር ዝመት፣

_ መከላከያን ደግፍ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም