ምክር ቤቱ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ 11ኛ ክልል ሆኖ እንዲደራጅ ወሰነ

66

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 20/2014(ኢዜአ) የፌዴሬሽን ምክር ቤት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በህዝበ ውሳኔ ውጤት መሰረት 11ኛ ክልል ሆኖ እንዲደራጅ ወሰነ።

ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 6ኛ የፓርላማ ዘመን 1ኛ ዓመት የስራ ጊዜ 1ኛ አስቸኳይ ስብሰባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝበ ውሳኔ ውጤትን መርምሮ አጽድቋል።

ምክር ቤቱ ህዝበ ውሳኔውን ያጸደቀው የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰበሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ሪፖርት ካቀረቡ እና የማንነት፣ የአስተዳደር ወሰንና የሰላም ግንባታ ቋሚ ኮሚቴ ለምክር ቤቱ የውሳኔ ሃሳብ ካቀረበ በኋላ ነው።

ምክር ቤቱ በቀረበው የውሳኔ ሀሳብ ላይ ከተወያየ በኋላ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ 11ኛ ክልል ሆኖ እንዲደራጅ በሙሉ ድመጽ አጽድቋል።

በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የሚገኙ አምስት ዞኖችና አንድ ወረዳ ራሳቸውን ችለው በክልልነት ለመደራጀት መስከረም 20 ቀን 2014 ዓ.ም ሕዝበ ውሳኔ ማካሄዳቸው ይታወሳል።

ለህዝበ ውሳኔው በተካሄደው ድምፅ አሰጣጥ አምስቱ ዞኖች እና አንዱ ልዩ ወረዳ አንድ የጋራ ክልል መመሥረቱን ደግፈው 1 ሚሊዮን 221 ሺህ 92 ድምፅ ሰጥተዋል።

በአንጻሩ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል አካል ሆነው መቀጠልን ደግፈው 24 ሺህ 24 ድምጽ መስጠታቸው ይታወቃል።

የተካሄደውን የህዝበ ውሳኔ ውጤት ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ለፌዴሬሽን ምክር ቤት በደብዳቤ ማሳወቁም ይታወሳል።

በውጤቱ መሠረት የፌዴሬሽን ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ፤የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ባካሄደው ህዝበ ውሳኔ ውጤት መሰረት በ11ኛ ክልልነት እንዲደራጅ ወስኗል።

ምክር ቤቱ ከተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት አንዱ የብሔር ብሔረሰቦችን የራስን ዕድል በራስ የመወሰን ወይም ራስን በራስ የማስተዳዳር ጥያቄዎች ሕገ-መንግስታዊ እልባት መስጠት ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም