ኢትዮጵያን ሲያደማ የቆየውን ወራሪ ኃይል የማጥፊያው ጊዜ አሁን ነው

86

መኮንን ከበደ ነዋሪነቱ በአሜሪካ አትላንታ ግዛት ጆርጂያ ነው።

ዛሬ ግን ቅንጡ ኑሮውን በመተው ለአገር ሕልውና መከበር ተጋድሎ እያደረጉ ካሉት የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች ጋር አሸባሪውን ህወሃት ለመፋለም በወሎ ግንባር ተገኝቷል።

"ዜጎቿን በመጨፍጨፍ ኢትዮጵያን ሲያደማና ሲዘርፍ የቆየውን ወራሪ ኃይል የማጥፊያው ጊዜ አሁን ነው" የሚለው መኮንን፤ ለአገሩ ሕልውና መከበር እየተካሄደ ያለውን ትግል ተቀላቅሏል።

በስፍራው የመገኘቱ ዓላማ በዜጎች ላይ ሰቆቃ እየፈጸመ የሚገኘውን የህወሓት ሽብርተኛ ኃይል በወሎ ምድር ታሪክ ሆኖ እንዲቀር መፋለም እንደሆነም ተናግሯል መኮንን።

በወሎ ግንባር ኢትዮጵያን አትንኩ ያሉ የቁርጥ ቀን ልጆች በአገር ሉዓላዊነት ላይ አደጋ የፈጠረውን አሸባሪ ወራሪ ኃይል ግብዓተ መሬት ለመፈጸም በቁርጠኝነት ይታገላሉ ብሏል።

እንደ መኮንን ሁሉ በወሎ የተገኙ ወጣቶች ኢትዮጵያን ለማፍረስ ወሎን መሸጋገሪያ ለማድረግ የሚሞክረውን አሸባሪው ህወሃት መቀበሪያውን እዚሁ እናደርገዋለን ሲሉ ተናግረዋል።

ወጣቶቹ አሸባሪውን ወራሪ ለመደምሰስ እየተፋለመ ለሚገኘው ሠራዊት ደጀንነታቸውን ለማሳየት በደሴ ከተማ ከነዋሪዎች ጋር የአደባባይ ትዕይንት ላይ ተሳትፈዋል።

ወጣቶቹ አሸባሪውን ህወሃት በወሎ ምድር ለመቅበር እስከ ሕይወት መስዋዕትነት ለመክፈል ያላቸውን ቁርጠኝነትም አረጋግጠዋል።

ወጣቶቹ አሸባሪው የህወሓት ወራሪ ኃይል ከህፃን እስከ አዋቂ ሕዝቡን አነሳስቶ የፈጸመውን ወረራ በሚመጥን ልክ በመደራጀት መፋለም እንደሚገባም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም