አዲስ የተሰየመው ካቢኔ የተሻለ ውጤት ማምጣት የሚያስችለውን አደረጃጀት የያዘ ነው

69

ሶዶ፤ መስከረም 26/2014 (ኢዜአ)፡ አዲስ የተሰየመው ካቢኔ በትምህርት ዝግጁነትም ሆነ በልምድ የካበተ አቅም ያላቸውና ለአገርና ለህዝብ የተሻለ ሰርተው ለውጥ የሚያመጡ ተሿሚዎችን ያካተተ መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ።

የካቢኔ አባላቱ በሰላምና መረጋጋት ላይ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባም ጠቁመዋል።

በዩኒቨርሲቲው የህግ መምህር አቶ አብነት ጨመረ ለኢዜአ እንዳሉት በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተሰየመው ካቢኔ አባላት በቂ የትምህርት ዝግጅትና ልምድ ያላቸው ለአገርም የተሻለ ነገር መስራት የሚችሉ ናቸው።

የካቢኔ አባላቱ ለህዝብና ለአገር ጥቅም ቅድሚያ በመስጠት የተጣለባቸውን ከባድ ሃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።

ከተመደቡበት ተቋም ባለፈ ህዝብን በማስተባበር በአገሪቱ ሰላምና መረጋጋትን ለማምጣት መስራት  እንዳለባቸውM ገልጸዋል።

አስፈፃሚ አካላት በተመደቡበት ተቋም  ስር የሚከናወኑ ስራዎች በአግባቡ መፈጸማቸውን በመከታተል  የህብረተሰቡን ጥያቄ በአግባቡ መመለስ እንዳለባቸው አስረድተዋል። 

በዩኒቨርሲቲው የህዝብ አስተዳደርና ልማት ትምህርት ክፍል ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር አሜን ደበበ ተሿሚዎቹ ያላቸውን የትምህርት ዝግጁነትና የካበተ ልምድ በመጠቀም ለአገርና ለህዝብ አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።

ተተኪ አመራር ከማፍራት አንጻርም በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።

ዛሬ በተካሄደው ስድስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አንደኛ ልዩ ስብሰባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የካቢኔ አባላትን ሹመት ማስጸደቃቸው የሚታወስ ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም