ለትምህርት ጥራት ልዩ ትኩረት በመስጠት ዕውቀት መር ትውልድ ለመፍጠር ይሰራል

80

መስከረም 26 / 2014 (ኢዜአ) "በኢትዮጵያ ለትምህርት ጥራት ልዩ ትኩረት በመስጠት ዕውቀት መር ትውልድ ለመፍጠር እንሰራለን" ሲሉ የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ባዋቀሩት ካቢኔ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ፓርቲ መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የትምህርት ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል።

ከሹመታቸው በኋላ ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራሪያ "በኢትዮጵያ የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋትና ጥራቱን ለማስጠበቅ በልዩ ትኩረት ለመስራት ተዘጋጅተናል" ብለዋል።

በተለይም በትምህርት ስርዓቱ ላይ የሚታዩ መሰረታዊ የጥራት ችግሮችን ለይቶ "መፍትሔ መስጠትና የዜጎችን ህይወት ማሻሻል ተቀዳሚው ተግባራችን ይሆናል" ብለዋል ሚኒስትሩ።

በኢትዮጵያ የትምህርት መስክ "እውቀት መር ትውልድ ለመፍጠር ወሳኝ ምዕራፍ ላይ እንገኛለን" ብለዋል።

''የዚህን አገር ትምህርት በመሰረታዊነት መልኩ መቀየር የምንችልበትና ጥራቱን አሁን ካለበት በጣም በከፍተኛ ደረጃ የወደፊቱን ዕውቀት መር የሆነ ኢኮኖሚ ሊያግዝ የሚችል አዲስ ትውልድ በሰፊው መፍጠር አለብን” ሲሉም ገልጸዋል።

የተለያዩ የፖለቲካ አመለካከቶች ቢኖሩም በአገርና በህዝብ ጉዳዮች ያለ ልዩነት መስራት ግዴታ መሆኑንም ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ አሁን የተጋረጠባትን ፈተና እንድታልፍ ከፖለቲካ ልዩነት በላይ በአገር ጉዳይ አብሮ መቆም እንደሚጠይቅ ጠቅሰዋል።

የአገር ሉዓላዊነትና ቀጣይነት ጉዳይ ሚዛን የሚደፋ በመሆኑ "አገርን ከችግር ማሻገር የሁላችንም ሃላፊነት ነው" ሲሉ ገልጸዋል።

የተፎካካሪ ፓለቲካ ፓርቲ አመራር አባላት በተለያዩ ሃላፊነቶች መሾማቸው የኢትዮጵያ ፖለቲካ "በመተመማን ላይ የተመሰረተ ትብብር ለመፍጠር የሚያስችል መሆኑን በተግባር እያሳየ ነው" ብለዋል።

የፖለቲካ አመለካከት ልዩነቶች እንዳሉ ሆነው በአገር ጉዳይ ግን በጋራ መቆምና ችግሮችንም በጋራ መፍታት የጋራ ሃላፊነት መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም