ቀጥታ፡

በጠቅላይ ሚኒትስር ዶክተር አቢይ አህመድ የተጎበኙት ጋና እና ሴኔጋል በጥቂቱ

በሚዲያ ሞኒተሪግና ትንተና ዳይሬክቶሬት (ኢዜአ)

ሴኔጋል እና ጋና ልክ እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ የብዝሃ ህዝብ፣ ብሔር፣ ቋንቋ እና እምነቶች እና ሀይማኖቶች ባለቤት ከመሆናቸው ባሻገር ሰላማዊ የዲሞክራሲ ሽግግር ከሚከናወንባቸው ሀገራት መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አቢይ አህመድ በሴኔጋል እና በጋና ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገዋል፡፡ እነዚህ ሁለቱ ሀገራት ከኢትዮጵያ ጋር የሚያመሳስላቸው በርካታ ታሪክ ያላቸው ሀገራት ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል  እንደ ሀገር ነጻነታቸውን ካረጋገጡ በኋላ ለአፍሪካ ሀገራት ነጻነት እና ለአፍሪካ ህብረት መጠናከር ያበረከቱት አስተዋጽኦ ተጠቃሽ ነው፡፡

ለጋና ብሎም ለአፍሪካ ነጻነት ከታገሉት ቀደምት ስመ-ጥር ጋናውያን መካከል የጋና የነጻነት አባት የሚባሉት ኩዋሜ ንኩርማህ ሲሆኑ ሀገሪቱን እኤአ ከ1957 እስከ 1966 ቀደም ሲል በጠቅላይ ሚኒስትርነት ቀጥሎም በፕሬዚደንትነት አገልግለዋል፡፡

ሴኔጋል እና ጋና በምዕራብ አፍሪካ ተጽዕኖ ፈጣሪ እና በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይም በትብብር በመስራት ጠንካራ ልምድ ካላቸው የአፍሪካ ሀገራት መካከል በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ፡፡ በዚህም የቡድን 24ን ጨምሮ በበርካታ አካባቢያዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ድርጅቶች ውስጥ ንቁ ተሳታፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡

ሁለቱም ሀገራት በፕሬዚደንት የሚመራ ህገ-መንግስታዊ አሃዳዊ ዲሞክራሲን እና የመንግስት ውቅር የሚከተሉ ሀገራት ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በ10 ክልሎች እና በሁለት የከተማ መስተዳድሮች የተዋቀረች እና የክልል ምክር ቤቶች አባላት በቀጥታ በህዝቡ እንደሚመረጡ ሁሉ፤ ጋና በ16 ክልሎች እንዲሁም ሴኔጋል በ14 ክልሎች የተዋቀሩ ሲሆኑ የክልል ምክር ቤት አባላት ልክ እንደ ኢትዮጵያ በቀጥታ በህዝቡ የሚመረጡ ናቸው፡፡

ሁለቱም ሀገራት በአፍሪካ አህጉር ነጻ እና የተረጋጋ የመንግስት ስርዓት ካላቸው ሀገራት መካከል በቀዳሚነት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ጋና ልክ እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ በተፈጥሮ የማዕድን ሀብት ባለቤት መሆኗ የሚታወቅ ሲሆን በጤና ስርዓት፣ በኢኮኖሚ ዕድገት እና በሰብዓዊ ልማት ላይ ጠንካራ ውጤቶችን ማስመዝገቧን መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡

ጋና ከአፍሪካ ሀገራት መካከል በልማት ቀዳሚ የሚያደርጋትን እኤአ ከ2020 እስከ 2029 ድረስ የሚተገበር የልማት ዕቅድ አዘጋጅታ እየተገበረች ሲሆን በተጨማሪም እኤአ ከ2030 እስከ 2039 ድረስ በሀገሪቱ የኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚን ማረጋገጥ የሚያስችል የረዥም ጊዜ ትልም ነድፋ እየተንቀሳቀሰች መሆኑ ከኢትዮጵያ የ10 ዓመት የልማት እና የብልጽግና ዕቅድ ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው፡፡

የሶስቱ ሀገራት የኢኮኖሚ መሰረት እና ለዜጎቻቸው የስራ ዕድል ከሚፈጥሩባቸው ዘርፎች መካከል የማዕድን ልማት፣ የግንባታ፣ የቱሪዝም ልማት እና ግብርና መሆናቸው ሀገራቱ ተመሳሳይ የማደግ ፍላጎት እና ተቀራራቢ ትልም እንዲቀርጹ እና ለውጤታማነቱም በጋራ እንዲሰሩ መልካም መንገድ የሚከፍት ነው፡፡  ሶስቱ ሀገራት ለፓን አፍሪካኒዝም መጠናከር የየራሳቸውን ሚና የተወጡ ሀገራት ናቸው፡፡

ይህ ጉብኝት ኢትዮጵያ ከጋና እንዲሁም ከሴኔጋል ጋር የአፍሪካ ህብረት እንዲቋቋም ባስቻለው የፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ መነሻነት የበለጠ የሁለትዮሽ እና በአፍሪካዊ ጉዳዮች ላይ በቅርበት እና በጋራ ለመስራት የሚያስችል መግባባት የተደረሰበት እንደነበር ተገልጿል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም