በትግራይ ክልል በስምንት የተለያዩ አካባቢዎች ሲንቀሳቀስ የነበረ የሽፍታ ቡድን እርምጃ ተወሰደበት ... ሌተናል ጄኔራል ባጫ ደበሌ

97

ሚያዝያ 5/2013(ኢዜአ) በትግራይ ክልል በስምንት የተለያዩ አካባቢዎች ሲንቀሳቀስ የነበረ የሽፍታ ቡድን በአገር መከለከያ ሰራዊት እርምጃ እንደተወሰደበት ሌተናል ጄኔራል ባጫ ደበሌ ገለጹ።

የመከላከያ የግንባታ ስራዎች ዋና አስተባባሪ ሌተናል ጄኔራል ባጫ ወቅታዊ ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

መግለጫቸውም በትግራይ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች በሚንቀሳቀሰው የህወሃት ጁንታ ታጣቂ ላይ የሀገር መከላከያ ሰራዊት በወሰደውን እርምጃ በስምንት የተለያዩ አካባቢዎች ሲንቀሳቀስ የነበረውን የታጠቀ ሃይል ደምስሷል ነው ያሉት።

ወንጀለኞችን በማደኑ ሂደት በርካቶችን በቁጥጥር ስር ማዋሉንም ገልጸዋል።

እርምጃ የተወሰደባቸውና በቁጥጥር ስር የዋሉት ታጣቂዎች በዋጅራት፣ አፅቢ፣ ሀቄመሳል፣ ደስአ፣ ቦራ፣ ፅጌረዳ፣ ውቅሮማርያም፣ ዛና፣ ሃውዜንና ሌሎች አካባቢዎች ሲንቀሳቀሱ እንደነበር አስታውሰው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ባደረገው አሰሳ መሆኑን ገልጸዋል።

እንደ ሌተናል ጄኔራል ባጫ ገለፃ እርምጃው የተወሰደባቸው የጁንታውን አመራሮች ለመጠበቅ በተጠቀሱት አካባቢዎች ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ታጣቂዎች ናቸው።

የሀገር መከላከያ ሰራዊት በወሰደው እርምጃ የጁንታው ድብቅ ትንንሽ ማሰልጠኛዎችም ሙሉ በሙሉ ሲወድሙ በርካቶች የቡድኑ ታጣቂዎች  እጃቸውን ሰጥተዋል ብለዋል።

በቀጣይም እስካሁን ያልተያዙትን የጁንታው መሪዎች ሰራዊቱ ለመቆጣጠር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

ቀሪ የጁንታው መሪዎች ከሀገር ለመውጣት ሞክረው የነበረ ቢሆንም የሀገር መከላከያ ሰራዊት የማይደርስበት አካባቢ ባለመኖሩ እንዳልተሳካላቸው ተናግረዋል።

በኦሮሚያ ክልል በዜጎች ላይ ጥቃት እየፈፀሙ የነበሩ ቡድኖች ላይም ጠንካራ እርምጃ መወሰዱን ሌተናል ጄኔራል ባጫ አስታውሰዋል።

በሱዳንና በኢትዮጵያ መካከል ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ ተጠይቀው ሌተናል ጀነራል ባጫ በሰጡት ማብራሪያም "ኢትዮጵያ ሁሌም ለሰላም አማራጭ ቅድሚያ ትሰጣለች" ያሉ ሲሆን "ይህ ማለት ግን ሀገራችንን ለመጠበቅ ዝግጁ አይደለንም ማለት አይደለም" ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም