የፌዴራል ታክስ ይግባኝ ኮሚሽን በስድስት ወራት ለ297 መዝገቦች ውሳኔ ሰጥቷል

80

አዲስ አበባ፣ የካቲት 2 / 2013 (ኢዜአ) የፌዴራል ታክስ ይግባኝ ኮሚሽን በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ከቀረቡለት ቅሬታዎች ለ297 መዝገቦች ውሳኔ መስጠቱን ገለፀ።

ኮሚሽኑ በ2013 በጀት ዓመት የስድስት ወር ዕቅድ አፈፃፀሙ ላይ ከሰራተኞቹ ጋር ሲወያይ አፈፃፀሙ 'የተሻለ' እንደሆነ ተገልጿል።

የኮሚሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉጌታ አያሌው እንደገለጹት፤ ባለፉት ስድስት ወራት 677 የታክስ ይግባኝ ቅሬታዎች ቀርበዋል።

ከእነዚህ ቅሬታዎች መካከል ለ310 መዝገቦች ቀጠሮ በማስያዝ ለ297ቱ ውሳኔ በመሰጠቱ 13 መዝገቦች ብቻ መቅረታቸውን ገልጸዋል።

የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በአንድ ጊዜ በርካታ የቅሬታ መዛግብቶች እንዳይታዩ ተግዳሮት ቢሆንም የኮሚሽኑ ውሳኔ የመስጠት አቅም 96 በመቶ መድረሱን አቶ ሙሉጌታ አመላክተዋል።

"በውሳኔው መሰረት ለንግዱ ማኅበረሰብ ተወስኖለት ከሆነ ያስያዘው ገንዘብ የሚመለስ ሲሆን ለመንግስት ከተወሰነም ገንዘቡ ለልማት ስራ የሚውል ይሆናል" ብለዋል።

ኮሚሽኑ ለቀረቡ የቅሬታ መዛግብት ውሳኔ ከመስጠት ጎን ለጎን ተቋሙን የማደራጀትና መመሪያዎችን የማውጣት ተግባራት ማከናወኑን ገልፀዋል።

ወደ ኮሚሽኑ የሚመጡ ቅሬታዎችን ጉዳይ ለይቶ ለማወቅና የሚሰጡ ውሳኔዎች ወጥነት እንዲኖራቸው ባለፉት ስድስት ወራት መስፈርት መዘጋጀቱን ተናግረዋል።

ኮሚሽኑ በቀጣይም በበይነ መረብ አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ዳታ ቤዝ በማስገንባት ላይ እንደሆነ አቶ ሙሉጌታ ጠቁመዋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም