የኢትዮጵያ የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ለሶስት ተቋማት እውቅና ሰጠ

93

አዲስ አበባ ጥር 13/2013 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ ህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም በመረጃ ተደራሽነት መልካም አፈፃፀም ላሳዩ ሶስት ተቋማት እውቅና ሰጥቷል።

ተቋሙ እውቅና የሰጠው ለጤና ሚኒስቴር፣ ለኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩትና ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዓለም አቀፍ ልማት ፕሮግራም (ዩ.ኤን.ዲፒ) ነው።

ዕውቅናውን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈጉባኤ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ ለተቋማቱ የስራ ሀላፊዎች አበርክተዋል።

ተቋማቱ እውቅና የተሰጣቸው በኢትዮጵያ የኮሮና ቫይረስ ከተከሰተ ጀምሮ የበሽታውን ስርጭት ለመግታት መረጃዎችን ወደ ህዝብ በማድረስ ረገድ ባበረከቱት አስተዋጽኦ መሆኑን የኢትዮጵያ የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ዋና ጠባቂ ዶክተር እንዳለ ሀይሌ ተናግረዋል።

እውቅናው ሌሎች ተቋማት መረጃ በማድረስ ረገድ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ተነሳሽነት እንደሚፈጥርም ጨምረው ገልጸዋል።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈጉባኤ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ በበኩላቸው ሁሉም ተቋማት ትክክለኛና ተጨባጭ መረጃ ለህብረተሰቡ ማድረስ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም