መንግስት በትግራይ ክልል የታወጀውን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመጠቀም የመተከል ዞን የጸጥታ ችግርን እንዲፈታ ምክር ቤቱ አሳሰበ

86

አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2013(ኢዜአ) መንግስት በትግራይ ክልል የታወጀውን አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመጠቀም የመተከል ዞን የጸጥታ ችግርንም ሊፈታ እንደሚገባ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሳሰበ።

በመተከል ዞን የንጹሃን ዜጎች ግድያ፣ አካል ጉዳትና መፈናቀል ሊቆም ያልቻለው ድብቅ የፖለቲካ ዓላማ ባላቸው አካላት እንደሆነም የምክር ቤቱ አባላት አንስተዋል።

የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 8ኛ መደበኛ ስብሰባ በውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች እንዲሁም የህግ፣ ፍትህና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎች በመተከል ዞንና በሌሎች አካባቢዎች የተፈጸመውን የዜጎች ግድያ አስመልክቶ በቀረበለት የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተወያይቷል።

ቋሚ ኮሚቴዎች በምርምራ ሂደታቸው በደረሱባቸው ዋና ዋና ጭብጦች በመተከል ዞንና በሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች በተከሰተው የጸጥታ ችግር ማንነትን መሰረት ያደረገ የንጹሃን ዜጎች ህይወት መቀጠፉን፣ የአካል ጉዳትና ንብረት ውድመት መድረሱ ተነስቷል።

የተፈጠረው ችግር የተወሳሰበና በፍጥነት ሊቆም ያልቻለው የፖለቲካ ዓላማ ባለቸው አካላት ስለመሆኑ ቋሚ ከሚቴዎቹ አስረድተዋል።

የውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ነገሪ ሌንጮ፤ እንደገለጹት መንግስት ባለፉት ሁለት ዓመታት የዴሞክራሲ ምህዳርን ለማስፋት አሳሪ ሕጎችን የማሻሻልና አዳዲስ ሕግጎችን በማውጣት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ጥረት አድርጓል።

ለውጡ ያልተዋጠላቸው የጥፋት ሃይሎች ግን በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች ለሚፈጠሩ ግጭቶችና ለንጹሃን ዜጎች ሕይወት ማለፍ ምክንያት ሆነዋል።

በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ህዝብና መንግስት የጣለባቸውን ሃላፊነት ወደ ጎን በመተው ከጥፋት ሃይሎች ጋር በማበር ችግሩ እንዲባባስ ማድረጋቸውንም ጠቅሰዋል።

በመተከል ዞን የሕግ የበላይነትን በማረጋገጥ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን መንግስት በትግራይ ከልል የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመጠቀም ችግሩን ሊፈታ ይገባዋል ብለዋል።

የምክር ቤቱ አባላት ቋሚ ኮሚቴዎቹ ካነሷቸው የውሳኔ ሃሳቦች በተጨማሪ መፍትሄ ያሏቸውን ሌሎች ሃሳቦች አንሸራሽረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም