ኒውዮርክ ከተማ ከፕሬዚደንት ትራምፕ ኩባንያ ጋር ያላትን የስራ ስምምነት ልታቋርጥ ነው


ጥር 6/2013 (ኢዜአ) የአሜሪካዋ ኒውዮርክ ከተማ አስተዳደር ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ በስልጣን ላይ እያሉ ለሁለት ጊዜያት መከሰሳቸውን ተከትሎ ፕሬዚደንቱ በባለቤትነት ከሚያስተዳደሩት ኩባንያ ጋር ያለውን የስራ ግንኙነት
ልታቋርጥ እንደሆነ አስታወቀች።

ባለፈው ሳምንት በአሜሪካ የተከሰተውን ሁከት ተከትሎ የፕሬዚደንቱ ግላዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ቀውስ ውስጥ መግባታቸውና ከየአቅጣጫውም ወቀሳ እየበረታባቸው መሆኑ ይታወቃል፡፡

የፕሬዚደንቱ ካምፓኒ በኒውዮርክ ከተማ ለሚገኘው ማዕከላዊ ፓርክ ሁለት የበረዶ መንሸራተቻ ሜዳዎች፣ የመዝናኛ ተሸከርካሪ መቀመጫዎችን እና የጎልፍ ሜዳዎችን ማቅረብ የሚያስችለው ስምምነት እንደነበረው ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

ይህ የስራ ስምምነት ለድርጅቱ በዓመት 17 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ወይም 12 ነጥብ 5 ሚሊየን ዩሮ የሚስገባ እንደነበር  ተጠቅሷል፡፡

ከተማዋ ከትራምፕ ድርጅቶች ጋር በጋራ መስራት እንደምታቆም የኒው ዮርክ ከተማ ከንቲባ ቢል ዴ ብላሲዮ መናገራቸውም በዘገባው ተመላክቷል፡፡

ከንቲባው አክለውም ይህን ውሳኔ ለመወሰን የህግ አማራጮችን እያጤኑ መሆኑንም ጠቁመዋል።

እንደ መረጃው ከሆነ ባለፈው ሳምንት በዋና ከተማዋ የተከሰተውን ሁከት ተከትሎ በርካታ የፖለቲካ ድጋፍ አድራጊዎችና ነጋዴዎች ራሳቸውን ከፕሬዚዳንቱ እና ከንግድ ድርጅቶቻቸው እየራቁ መሆናቸውም በዘገባው ተጠቅሷል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም