የፌደራል መንግስት ከትግራይ ክልል መንግስት ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንዳያደርግ ውሳኔ ተላለፈ

60

አዲስ አበባ መስከረም 26 /2013 (ኢዜአ) የፌዴሬሽን ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ጉባዔ የፌደራል መንግስት ከትግራይ ክልል መንግስት ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንዳያደርግ ውሳኔ አሳለፈ፡፡

ይህ ውሳኔ ሊተላለፍ የቻለው ባለፈው ነሃሴ 30 2012 ዓ.ም የፌዴሬሽን ምክር ቤት አድርጎት በነበረው አስቸኳይ ጉባዔ በትግራይ ክልል የሚካሄደው ምርጫ እንዳልተደረገ፣ እንዳልተፈጸመ እና እንደማይጸና ውሳኔ ማስተላለፉን ተከትሎ ነው፡፡

ውሳኔውን የሚከታተል የህገ መንግስት ጉዳዮች እና የማንነት ጉዳዮች አጣሪ ቋሚ ኮሚቴ ጉዳዩን ሲከታተል ቆይቶ ውሳኔው ባለመፈጸሙ ባዛሬው ዕለት ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ነው ይህንን ወሳኔ ሊያሳልፍ ያቻለው፡፡

ምክር ቤቱ በትግራይ ክልል መንግስት ላይ ሶስት ውሳኔዎችን ማሳለፉን ገልጿል፡፡

የመጀመሪያው የትግራይ ክልል ያካሄደውን ኢ-ህገ መንስታዊ ምርጫ ተከትሎ ከተመሰረቱ የትግራይ ክልል ምክር ቤትና ከፍተኛ የህግ አስፈጻሚ አካል ጋር የፌዴራል መንግስት ምንም አይነት ግንኙነት እንደማያደርግ ወስኗል፡፡

ሁለተኛው የፌደራል መንግስት የትግራይ ህዝብን የልማትና መሰረታዊ አገልግሎቶች ፍላጎት ማዕከል በማድረግ የከተማ እና የቀበሌ አስተዳደርን ጨምሮ በክልሉ ከሚገኙ ህጋዊ ተቋማት ብቻ የስራ ግንኙነት ያደርጋል፡፡

ሶስተኛ የውሳኔውን አፈጻጸም በፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ እና ጉዳዩ በሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴ ክትትል መደረግ እንዳለበት ውሳኔ ተላልፏል፡፡

(EBC)

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም