የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20 /2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል::
የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ በሀዋሳ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና መካከል ዛሬ ይደረጋል።
የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይከናወናል።
ሀዋሳ ከተማ በሩብ ፍጻሜው አርባ ምንጭ ከተማን 2 ለ 0 እንዲሁም ኢትዮጵያ ቡና ፋሲል ከነማን 4 ለ 1 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜው ማለፋቸው ይታወቃል።
በአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉ የሚመራው ሀዋሳ ከተማ በዘንድሮው የኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር የመጀመሪያ ሁለት ጨዋታዎች ቤንች ማጂ ቡና እና መቻልን አሸንፏል።
ክለቡ በኢትዮጵያ ዋንጫ እስከ አሁን ባደረጋቸው 3 ጨዋታዎች 7 ግቦችን ከመረብ ሲያሳርፍ 1 ጎል አስተናግዷል።
ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ በዚህ ውድድር አስቀድሞ ባደረጋቸው ጨዋታዎች ወልዲያ እና ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማን ማሸነፉ ይታወቃል።
በአሰልጣኝ ነጻነት ክብሬ የሚመሩት ቡናማዎቹ በውድድሩ ባደረጓቸው 3 ጨዋታዎች 10 ጎሎችን ሲያስቆጥሩ የተቆጠረባቸው 1 ግብ ብቻ ነው።
የሁለቱ ክለቦች አሸናፊ ከወላይታ ድቻ በፍጻሜው የሚገናኝ ይሆናል።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ትናንት በተደረገው የመጀመሪያ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ወላይታ ድቻ ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ ማለፉ ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊ በቀጣዩ ዓመት በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ኢትዮጵያን ወክሎ ይሳተፋል።