ቀጥታ፡

በአማራ ክልል በ43 ከተሞች የኮሪደር ልማት እየተካሄደ ነው

አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018(ኢዜአ)፦የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች በወልድያ ከተማ ሰፊ የኮሪደር ልማት ስራዎችን በምሽት ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አሕመዲን መሐመድ (ዶ/ር)፤ ወልድያ በርካታ ከተሞችን የምታገናኝ በመሆኗ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቱ ስትራቴጂካዊ እሴቷን ከፍ እንዳደረገው ገልጸዋል።

ቀደም ሲል የነበሩ ጎስቋላና ጠባብ ስፍራዎች ተወግደው፣ ምቹ ድልድዮችና ሰፋፊ የመዝናኛና የንግድ ቦታዎች ተከፍተዋል ነው ያሉት።


 

ኮሪደር ልማት ከውበት የዘለለ የትውልድና የሀገር ግንባታ ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፥ዛሬ በእነዚህ መንገዶች ላይ የሚንሸራሸሩ ህጻናት ነገ ሀገር የሚረከቡ በመሆናቸው ስራው ትውልድ ተሻጋሪ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።

የክልሉ ከተሞች ከወልድያ የፈጠራና የሀብት ቁጠባ ተሞክሮ ሊማሩ እንደሚገባ ተናግረዋል።

የአማራ ክልል የከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአሁኑ ወቅት በክልሉ በሚገኙ 43 ከተሞች ውስጥ ማዘጋጃ ቤቶችን ጨምሮ የኮሪደር ልማት እንቅስቃሴ በስፋት እየተካሄደ ይገኛል።

የክልሉ ከተሞች ከጎስቋላ ገፅታ ተላቀው ምቹ የሥራ፣ የመኖሪያና የቱሪዝም ሥፍራ እየሆኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል።


 

ወልድያ ከተማ በከፍተኛ ፍጥነትና በጥራት በመስራት አስደናቂ ለውጥ ማምጣቷን ገልጸዋል።

የከተማዋን ልማት ውስን ሀብትን በቁጠባና በጥራት የመጠቀምና ብዙ ሥራዎችን በፍጥነት የማሳካት ጥበብ በመከተል የመደመር መንግሥት ኢንተርፕረኒያል እሳቤን እየተገበረች መሆኑ ልዩ እንደሚያደርገው አብራርተዋል።

የወልድያ አመራርና ህዝብ ከተማችን ተጎሳቁላ አትኖርም በሚል የጋራ መግባባት ፈጥረው፣ ሀብት አሰባስበውና ፈጣን እርምጃ ወስደው የከተማዋን የኢኮኖሚ እሴት ከፍ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።

ይህም አመራር ከሕዝብ ጋር ተቀናጅቶ ከሠራ ማንኛውንም ተግዳሮት ማሸነፍ እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫና ለክልሉም ትምህርት የሚሰጥ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም