ማህበራት በመዲናዋ የኮሪደር ልማት ሥራዎች በመሰማራት ለሌሎች የሥራ ዕድል እየፈጠሩ ነው - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራት በመዲናዋ የኮሪደር ልማት ሥራዎች በመሰማራት ለሌሎች የሥራ ዕድል እየፈጠሩ ነው
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018 (ኢዜአ)፦በመዲናዋ የኮሪደር ልማት ስራ ላይ በመሠማራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለሌሎችም የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆኑን በከተማ ውበት፣ አረንጓዴ ልማትና ችግኝ አቅርቦት የተሰማሩ ማህበራት ገለጹ።
በአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት ለነዋሪዎችም ሆነ ለጎብኝዎች ምቹና ሳቢ የሆኑ በርካታ መዝናኛዎች፣ ፓርኮችና የመንገድ አካፋዮች ተገንብተው ለከተማዋ ልዩ ገጽታ እየፈጠሩ ይገኛሉ።
የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ውብና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉም ይነገራል።
ኢዜአ ያነጋገራቸው በመዲናዋ በከተማ ውበት፣ አረንጓዴ ልማትና ችግኝ አቅርቦት ላይ የተሰማሩ ማህበራት በስራቸው ውጤታማ ከመሆን ባለፈ ለሌሎችም የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ተናግረዋል።
በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 ነዋሪ የሆኑት ቀሲስ አዱኛ ጥጋቤ፤ በግልና በማህበር የተለያዩ ችግኞችን በማፍላት ለገበያ እያቀረቡ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በዚህም ለውበትና ለአረንጓዴ ልማት አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልፀው ማህበራቸው ከፍተኛ ገቢ እያመነጨ ከመሆኑም በላይ ለ40 ወጣቶች ጊዜያዊና ቋሚ የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰዋል።
በከተማ ውበትና አረንጓዴ እንክብካቤ ዘርፍ የተሰማሩት የውብዓለምና መሀመድ ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ውብዓለም ልባሴ፤ የኮሪደር ልማት የሥራ ዕድል ይዞላቸው እንደመጣ አስረድተዋል።
ከዚህ ቀደም ሥራ ስላልነበራቸው የባለቤታቸውን እጅ እየጠበቁ ይኖሩ እንደነበር በማውሳት፥ አሁን ላይ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል በመንገድ አካፋዮች የተተከሉ እፅዕዋትን በመንከባከብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል።
የአዲስ አበባ የስራና ክህሎት ቢሮ የስራ ስምሪት አገልግሎት ዳይሬክተር ሰብሀዲን ሱልጣን፤ ለስራ አጥ ወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።
መዲናዋን እንደ ስሟ ውብና ስማርት ሲቲ ለማድረግ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ለበርካታ ስራ አጥ ዜጎች ምቹ የስራ ዕድል ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል።
በዚህም 560 ማህበራት በከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ዘርፍ ተሰማርተው ለከተማዋ ውበትና ሳቢነት የድርሻቸውን በመወጣት ላይ ይገኛሉ ነው ያሉት።
በመዲናዋ እየተመዘገበ ላለው ፈጣን ልማትና እድገት ማህበራት ቁልፍ ሚና እየተጫወቱ በሥራ ዕድልም ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙ አመላክተዋል።