ቀጥታ፡

የግብርና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ስኬታማ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 3/2018 (ኢዜአ)፦ የግብርና ትራንስፎርሜሽን እቅዱን ስኬታማ ለማድረግ የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ።

ቋሚ ኮሚቴው የግብርና ሚኒስቴርን እና የተጠሪ ተቋማትን የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሶስት ወራት እቅድ አፈፃፀም ገምግሟል።

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዩች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ተቋማቱ ባለፉት ሶስት ወራት የግብርና ዘርፉን ለመለወጥ የሚያስችሉ ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን ገልፀዋል።

በተለይም የመኸር እርሻ ስራ እጅግ በተሻለ ዝግጅት የተከናወነ መሆኑን አመልክተው፤ በኩታ ገጠም እርሻና በሜካናይዜሽን እንዲሁ የተሻሉ ስራዎች መሰራታቸውን አንስተዋል።

በመኸር የስንዴ እርሻ፣ በሩዝ ምርት፣ በአኩሪ አተር እና የሆርቲካልቸር ዘርፎች የመጀመሪያው ሶስት ወራት አፈፃፀም ውጤታማ መሆኑን ለመገንዘብ ችለናል ነው ያሉት።

ከሌማት ትሩፋት ጋር ተያይዞም በወተት ምርት፤ በዶሮ እንቁላልና የማር ምርትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራትና የተገኘው ውጤት ተጠናክረው ሊቀጥሉ የሚገባው መሆኑን አንስተዋል።

ከእንስሳት ልማት አኳያም ዝርያን በማሻሻል፣ በቡና እና ሻይ ልማት የተገኘው የውጭ ምንዛሪ እድገት የተመዘገበበትና ውጤታማ ነው ብለዋል።

በዚሁ ወቅት የከተማ ግብርና ላይም ውጤታማ ስራዎች ተሰርተዋል ያሉት ሰብሳቢው፤ የሕብረት ስራ ማሕበራትን ውጤታማ ለማድረግ የተተገበሩ የሪፎርም ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸ ገልጸዋል።

የማዳበሪያ ስርጭት ላይ ባለፉት ሶስት ወራት ጥሩ ስራዎች የተሰሩ ሲሆን፤ ሃብቱን በአግባቡ ከማሰራጨትና ጥቅም ላይ ከማዋል አኳያ ቀሪ ስራዎች መኖራቸውን አመልክተዋል።

የግብርና ሚኒስትሩ አቶ አዲሱ አርጋ በበኩላቸው፤ ባለፉት ሶስት ወራት በተለይ የግብርና ዘርፉን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚያስችሉ ተግባራት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ገልፀዋል።

በሩብ ዓመቱ የሰብል ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ጋር ተያይዞ በበልግ ወቅት ሦስት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሔክታር መሬት በማረስ 78 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግት መቻሉን ጠቅሰዋል።

በመኸር እርሻም እንዲሁ 19 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ አፈፃፀሙ ከእቅድ በላይ 20 ነጥብ 6 ሚሊዮን ለማድረስ መቻሉን ተናግረዋል።

በሆርቲካልቸርና በጥጥ ምርትም ስኬታማ የሚባሉ ስራዎች መከናወናቸውን ነው ሚኒስትሩ ለአብነት የገለጹት ።

ከቋሚ ኮሚቴው የተሰጠው ግብዓት ግብርና ዘርፉን ውጤታማ አድርጎ ለመምራት የሚያስችል በመሆኑ ወደ ተግባር እንደሚለወጥ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም