ሀዋሳ ከተማን ለመኖሪያ፣ ለቱሪዝምና ለኮንፈረንስ ተመራጭ ለማድረግ ይሰራል-ከንቲባ ጥራቱ በየነ - ኢዜአ አማርኛ
ሀዋሳ ከተማን ለመኖሪያ፣ ለቱሪዝምና ለኮንፈረንስ ተመራጭ ለማድረግ ይሰራል-ከንቲባ ጥራቱ በየነ
ሀዋሳ ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ሀዋሳ ከተማን ለመኖሪያ፣ ለቱሪዝምና ለኮንፈረንስ ተመራጭ ከተማ ለማድረግ ከፍ ያለ ራዕይ በመሰነቅ ይሰራል ሲሉ አዲሱ የከተማዋ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ።
የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 2ኛ ዙር አስረኛ ዓመት 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤ አቶ ጥራቱ በየነን የከተማዋ ከንቲባ አድርጎ ሾሟል።
አዲሱ የከተማዋ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ ለምክር ቤቱ አባላት ባደረጉት ንግግር እንዳሉት፤ ከተሞችን የብልጽግና ማሳያ ለማድረግ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በአዲስ እሳቤ የተጀመረው የኮሪደር ልማት በሀዋሳ ከተማም እየተከናወነ ነው።
በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ በማስቀጠል ሀዋሳን ከአዲስ አበባ በመቀጠል በኢትዮጵያ ብሎም በአፍሪካ ለመኖሪያ፣ ቱሪዝምና ለኮንፈረንስ ተመራጭ ለማድረግ ከፍ ያለ ራዕይ ሰንቀን ያለመዘናጋት እንሰራለን ብለዋል።
ለዚህ ራዕይ ስኬት የመንግስት፣ የነዋሪውና የግል ሴክተሩ የተቀናጀና የተናበበ ስራ ወሳኝ መሆኑን ያነሱት አቶ ጥራቱ ሁሉንም ማህበረሰብ በማሳተፍ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።
የሀዋሳን በፍቅር ተከባብሮና ተደጋግፈው በወንድማማችነትና በአንድነት የሚኖሩባት የፍቅር ከተማነቷን ለማስቀጠል ጠንክረው እንደሚሰሩም ጠቁመዋል።
የከተማዋን ሰላምና ጸጥታ አጠናክሮ በማስቀጠል ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ እንድትሆን ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የሰላምና ጸጥታ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል።
ዓለም አቀፍ መስፈርቶችንና የከተማ ፕላንን መሰረት ባደረገ መልኩ በከተማዋ መሰረተ ልማቶችንና አረንጓዴ ስፍራዎችን የማስፋፋት ሥራ እንደሚሰራ ገልጸው፣ የሀዋሳ ሐይቅን ከብክለት የመጠበቅና የታቦር ተራራን ልማት በማፋጠን ለጎብኚዎች ምቹ የማድረግ ስራ ይሰራል ብለዋል።
የቆሻሻ አወጋገድና አያያዝን ከማዘመን ባለፈ ዘላቂ የከተማ ልማትን ተግባራዊ በማድረግ ንጹህና ምቹ ሀዋሳን ለመፍጠርም ትኩረት እንደሚሰጥ አመልክተዋል።
ሀዋሳ ከተማን ተመራጭ የቱሪዝምና የኮንፈረንስ መዳረሻ ለማድረግም ደረጃቸውን የጠበቁ የቱሪስት መዳረሻዎችን ቁጥር ከማሳደግ ባለፈ የከተማዋን የቱሪስት ሀብቶች ለማስተዋወቅ በትኩረት እንደሚሰራም አስታውቀዋል።
ከንቲባው በከተማዋ የኑሮ ውድነትን ለማቃለል የተጀመሩ የከተማ ግብርና የሌማት ትሩፋት መርሀግብሮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።
በስራ ዕድል ፈጠራ ለግሉ፤ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን በመፍጠር ሴቶች ወጣቶችና የተለያዩ ወገኖች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ የስራ አጥነትን ጫና ለማቃለል እንደሚሰራም አቶ ጥራቱ አስታውቀዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት በብልጽግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አብርሀም ማርሻሎ የቀረበለትን የአቶ ጥራቱ በየነን የከንቲባነት ሹመት በሙሉ ድምጽ ተቀብሎ በማጽደቅ ጉባኤውን አጠናቋል።