ቀጥታ፡

የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዘመናዊ አገልግሎቱን በፍጥነት ተደራሽ በማድረጉ ተጠቃሚ ሆነናል - ተገልጋዮች

አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 22/2018(ኢዜአ)፦ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዘመናዊ አገልግሎቱን በፍጥነት ተደራሽ በማድረጉ ተጠቃሚ ሆነናል ሲሉ ተገልጋዮች ገለፁ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ እንደገለጹት፤ የኢምግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት ለማሻሻል በተካሔደ ሪፎርም በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል።

በአሁኑ ወቅት በአገልግሎት በአንድ ዓመት ብቻ አራት ሚሊየን ፓስፖርት እንደሚቀርብ አመልክተው፤ በዘርፉ የተካሔደው ስር ነቀል የለውጥ ስራ ውጤታማ መሆኑን በተግባር የሚያሳይ ነው ብለዋል።

ከሶስት ዓመት በፊት የፓስፖርት አገልግሎት የማቅረብ አቅም ከ300 ሺህ ያልበለጠ እንደነበር ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያስተወሱት።

የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ተገልጋዮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ተቋሙ ረጅም ጊዜ ይወስድ የነበረውን አገልግሎት በማዘመን አድካሚ አሰራርን አስቀርቷል።

ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወይዘሮ ሩት ባንጃው፤ የፓስፖርት አገልግሎት ፍላጎታቸውን በኦንላይን በማጠናቀቅ ለመረከብ መምጣቸው ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት ተቋሙ እራሱን በማዘመን የተገልጋይ ጊዜ የሚቆጥብና እንግልት የሚያስቀር አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን በተጨባጭ ማየታቸውን ነው የሚገልጹት።

ቀደም ሲል የተቋሙን አገልግሎት ለማግኘት ረጅም ሰልፍና ቀናትን የሚወስድ ምልልስ ማድረግ ይጠበቅ ነበር ያለው ደግሞ ወጣት አስናቀ ሽመልስ ነው።

አሁን እየተሰጠ ያለው ቀልጣፋ የኢ-ፓስፖርት አገልግሎት ዘመናዊና ለተጠቃሚው ምቹ መሆኑን ነው ያረጋገጠው።

በተቋሙ አገልግሎቱን ለማግኘት የመጡት አቶ ረሺድ ሲራጅ በበኩላቸው፤ በተቋሙ በአግባቡ አገልግሎት ለማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል።

በኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የፓስፖርት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ሰሚራ ከሊፋ እንደገለጹት፤ ተቋሙ ከጥር 2017 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ ያደረገው የኢ-ፓስፖርት አገልግሎት ቀደም ብሎ ይነሱ የነበሩ ችግሮችን ያስቀረ ነው ብለዋል።

በአሁን ወቅት በቀን ስምንት ሺህ ያህል ለሚሆኑ ዜጎች የኦንላይን የፓስፖርት ምዝገባ እንደሚደረግ ገልጸው፤ ይህም የመልካም አስተዳደርና ብልሹ አሰራሮችን ለማስቀረት ያስቻለ ነው ይላሉ።

ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት ለአራት ሚሊየን ዜጎች መደበኛ እና አስቸኳይ ፓስፖርት ለመስጠት አቅዶ እየሰራ ሲሆን፤ ባለፉት ሶስት ወራትም ለ545 ሺህ ደንበኞች ፓስፖርት መውሰዳቸውን ገልፀዋል።

በአሁኑ ወቅት ተቋሙ በ12 ቅርንጫፎቹ አገልግሎቱን እየሰጠ መሆኑን አንስተው፤ በቀጣይም የቅርጫፎችን ብዛት 28 ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም