ቀጥታ፡
ስፖርት
ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Dec 2, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፀጋ ከድር በ43ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ከሁለት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ15 ነጥብ ደረጃውን ከ9ኛ ወደ 3ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ በውድድር ዓመቱ ምንም ጨዋታ አላሸነፈም።   በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሃ ግብር መቻል እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። አብዱልከሪም ወርቁ ለመቻል፣ መሐመድኑር ናስር ለድሬዳዋ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ኢሞሮ ማናፍ ከመቻል እና አቡበከር ሻሚል ከድሬዳዋ ከተማ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥተዋል። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ13 ነጥብ 5ኛ እንዲሁም ድሬዳዋ ከተማ በ11 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዘዋል። ምሽት 12 ሰዓት አዲስ አዳጊዎቹ ነጌሌ አርሲ እና ሸገር ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ታንዛንያ ከ17 ዓመት የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ዋንጫን አነሳች
Dec 2, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ፍጻሜ ጨዋታ ታንዛንያ ዩጋንዳን 3 ለ 2 አሸንፋለች። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ራዛኪ ምቤጌሌንዲ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሉክማን ምባላሳሉ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቶማስ ኦጌማ እና ብሪያን ኦልዋ ለዩጋንዳ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ታንዛንያ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ አሸናፊ ሆናለች። ዩጋንዳ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ሀገራቱ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ታንዛንያ 2 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። ታንዛንያ እና ብሩንዲ ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፋቸው ይታወቃል። ዛሬ በተደረገ የደረጃ ጨዋታ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ኬንያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፏን አረጋግጣለች። ከሕዳር 6 ቀን 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ሲካሄድ የነበረው የሴካፋ ማጣሪያ ዛሬ ፍጻሜውን አግኝቷል። በውድድሩ ከአንድ እስከ ሶስተኛ የወጡት ታንዛንያ፣ ዩጋንዳ እና ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2026 ሞሮኮ በምታስተናግደው 16ኛው ከ17 ዓመት የአፍሪካ ዋንጫ ሴካፋ ዞንን ወክለው ይሳተፋሉ። በአፍሪካ ዋንጫው 16 ሀገራት ተሳታፊ ናቸው።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ በማለፏ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Dec 2, 2025 137
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018(ኢዜአ)፦ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፉን ተከትሎ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በመልዕክታቸው ይህ እግር ኳስ ወዳድ ለሆነው ህዝባችን ትልቅ የድል ብስራት ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን (ቀይ ቀበሮዎቹ) ኬንያን 3 ለ 0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ ከ22 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ በማለፋቸው እንኳን ደስ አለን ሲሉም ገልጸዋል። በስፖርቱ ዘርፍ ታዳጊዎች ላይ በርትተን ከሰራን እግር ኳሳችን በአህጉራዊና በዓለም አቀፋዊ መድረኮች ከፍ የሚልበት ጊዜ ሩቅ እንደማይሆን ይህ ስኬት አመላካች ነው መሆኑንም ጠቅሰዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዛሬው ውጤት እንዲገኝ የበኩላቸውን ሚና ለተወጡ አካላትም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ አለፈች
Dec 2, 2025 111
አዲስ አበባ፤ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ከኬንያ አቻው ጋር ባደረገው የደረጃ ጨዋታ 3 ለ 0 በማሸነፍ ለአህጉራዊው መድረክ ማለፉን አረጋግጧል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ካሳው በ66ኛው ፤ አምበሉ ቢነያም አብርሃ በ79ኛው እና ብሩክ እይላቸው በ93ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ማለፏን ያረጋገጠች ሶስተኛ ሀገር ሆናለች። በውድድሩም ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች።   ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ2003 ስዊዚላንድ ባዘጋጀችው ውድድር ላይ ነበር። ከ22 ዓመታት በኋላ በውድድሩ ላይ ትሳተፋለች። ኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ላይ ስትሳተፍ የሞሮኮው ለአራተኛ ጊዜ ነው።   የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን አጥቂ ዳዊት ካሳው በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ስምንት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናቋል። ታንዛንያ እና ዩጋንዳ ሌሎች ለአፍሪካ ዋንጫው ያለፉ ሀገራት ናቸው።   የሴካፋ ማጣሪያ የፍጻሜ ጨዋታ በታንዛንያ እና ኬንያ መካከል ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይካሄዳል። በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ከሕዳር 6 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ዛሬ ይጠናቀቃል። በውድድሩ ላይ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የሚወጡ ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት መርሐግብር ዛሬ ይጠናቀቃል 
Dec 2, 2025 94
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የስምንተኛ ሳምንት መርሐግብር በመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአርባምንጭ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ባደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች አራት ጊዜ ድል ሲቀናው ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። ስድስት ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አራት ግቦችን አስተናግዷል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ12 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ስምንት ግቦች ደግሞ ተቆጥረውበታል። አርባምንጭ ከተማ በአራት ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌላኛው መርሃ ግብር አዲስ አዳጊዎቹ ነጌሌ አርሲ እና ሸገር ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነጌሌ አርሲ በሊጉ ካከናወናቸው ሰባት ጨዋታዎች ሁለቱን አሸንፎ በሁለቱ ተሸንፎ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ አምስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በዘጠኝ ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በበኩሉ ከስድስት ጨዋታዎች መካከል ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አራት ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ በተመሳሳይ አራት ግቦችን አስተናግዷል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ሸገር ከተማ በስምንት ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተመሳሳይ በዛሬው ዕለት መቻል ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በሊጉ ባካሄዳቸው ሰባት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 11 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል ሶስቱን ያሸነፈው ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በአንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስምንት ግቦችን አስተናግዷል። ድሬዳዋ ከተማ በ10 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ሶስተኛ አላፊ ሀገር ለመሆን ዛሬ ከኬንያ ጋር ወሳኝ ጨዋታ ታደርጋለች
Dec 2, 2025 96
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ከኬንያ አቻው ጋር የደረጃ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ከቀኑ 6 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በግማሽ ፍጻሜው በዩጋንዳ 3 ለ 0 መሸነፉን ተከትሎ ለአፍሪካ ዋንጫ የማለፍ የመጀመሪያ እድሉን ሳይጠቀም ቀርቷል። ቡድኑ ዛሬ ከኬንያ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ካሸነፈ ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፉን ያረጋግጣል። ተጋጣሚዋ ኬንያ በግማሽ ፍጻሜው በታንዛንያ 3 ለ 1 መሸነፏ የሚታወስ ነው።   ኢትዮጵያ እና ኬንያ በውድድሩ በምድብ አንድ የመጨረሻ ጨዋታ ተገናኝተው ኢትዮጵያ በዳዊት ካሰው ግብ 1 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1997 ቦትስዋና ባዘጋጀችው ውድድር ላይ ነበር። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ዛሬ ከኬንያ ጋር ለሶስተኛ ደረጃ እንዲሁም ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከሚያደርገው ወሳኝ ጨዋታ አስቀድሞ ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ልምምዱን ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የማጣሪያው የፍጻሜ ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ በታንዛንያ እና ዩጋንዳ መካከል ይደረጋል። ሁለቱ ሀገራት ለፍጻሜ ማለፋቸውን ተከትሎ እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ ለሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፋቸውን አረጋግጠዋል። ሁለቱ ሀገራት በማጣሪያው በምድብ ሁለት የነበሩ ሲሆን እርስ በእርስ ባደረጉት ጨዋታ ታንዛንያ ዩጋንዳን 2 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያዊው ኢንተርናሽናል ዳኛ ኤፍሬም ደበሌ የፍጻሜውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመራል።   በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ከሕዳር 6 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ዛሬ ይጠናቀቃል። በውድድሩ ላይ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የሚወጡ ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) መረጃ ያመለክታል። በሞሮኮ አስተናጋጅነነት በሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ራሷን ሞሮኮ ጨምሮ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በማሸነፍ መሪነቱን አጠናከረ 
Dec 1, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት መርሐግብር ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ብርሃኑ በቀለ በአራተኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ19 ነጥብ የሊጉን መሪነት አጠናክሯል። በሊጉ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በስምንት ነጥብ ከነበረበት 12 ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ሀዲያ ሆሳዕናን 1 ለ 0 ረቷል።   አቡበከር አዳሙ በ11ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ቡና በ10 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 10ኛ አሻሽሏል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሀዲያ ሆሳዕና በሰባት ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ምድረገነት ሽሬ ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ይጫወታል
Dec 1, 2025 136
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከመርሃ ግብሮቹ መካከል ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች አምስቱን ሲያሸንፍ ሽንፈት ያስተናገደው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 11 ግቦችን ሲያስቆጥር አራት ግቦችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ16 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። አንድ ጊዜ ሲሸነፍ አምስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ስምንት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ በተመሳሳይ ስምንት ግቦች ተቆጥረውበታል። ንግድ ባንክ በስምንት ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። በአንጻሩ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ከቀናው ወደ አሸናፊነት መንገድ ይመለሳል። በሌላኛው መርሃ ግብር ምድረገነት ሽሬ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ በውድድር ዓመቱ ባካሄዳቸው ሰባት ጨዋታዎች ሁለቱን አሸንፎ በሁለቱ ተሸንፎ ሶስት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በዘጠኝ ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል አራቱን በድል ሲወጣ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። በሰባቱ ጨዋታዎች ላይ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ጎሎች ገብተውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ13 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ኢትዮጵያ ቡና ከሀዲያ ሆሳዕና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ያሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና አራት ጊዜ ተሸንፏል። አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በጨዋተያዎቹ ላይ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር ስምንት ግቦችን አስተናግዷል። ቡናማዎቹ በሰባት ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ሀዲያ ሆሳዕና በሊጉ እስከ ማሸነፍ የቻለው አንድ ጨዋታ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሽንፈት ሲገጥመው በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ ከተጋጣሚው እኩል ሰባት ነጥብ በመሰብሰብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 16ኛ ደረጃን ይዟል።
በተጠባቂው ጨዋታ ቼልሲ እና የሊጉ መሪ አርሰናል አቻ ተለያዩ
Nov 30, 2025 167
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት ጨዋታ ቼልሲ እና አርሰናል አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ትሬቮህ ቻሎባህ በ48ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ቼልሲ መሪ ሆኗል። ሚኬል ሜሪኖ በ59ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል አርሰናል አቻ መሆን ችሏል። በጨዋታው ላይ የቼልሲው የአማካይ ተጫዋች ሞሰስ ካይሴዶ በ38ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ተሰናብቷል። ይህም በቡድኑ እንቅስቃሴ ላይ ተጽእኖ አሳድሯል። አርሰናል በጨዋታው ላይ ያገኘውን የቁጥር ብልጫ በሚገባ መጠቀም አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ በ24 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 30 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ዝቅ ብሏል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ሊቨርፑል ዌስትሃም ዩናይትድን 2 ለ 0፣ ማንችስተር ዩናይትድ ክሪስታል ፓላስን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። ብራይተን ኖቲንግሃም ፎረስትን 2 ለ 0 ሲረታ አስቶንቪላ ዎልቭስን 1 ለ 0 አሸንፏል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና አዳማ ከተማ አቻ ተለያዩ
Nov 30, 2025 121
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና አዳማ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተካሄዷል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ15 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ በበኩሉ በ13 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ባህር ዳር ከተማ ኢትዮጵያ መድንን በመሳይ አገኘሁ የፍጹም ቅጣት ምት 1 ለ 0 አሸንፏል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ መቀሌ 70 እንደርታን 1 ለ 0 በመርታት በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አስመዝግቧል። ጌትነት ተስፋዬ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ዳዊት ገብሩ በሁለት ቢጫ ካርድ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በሌላኛው መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ እና ወላይታ ድቻ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ዳግም አወቀ ለፋሲል ከነማ ፣ መሳይ ሰለሞን ለወላይታ ድቻ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የፋሲል ከነማው ቃልኪዳን ዘላለም በ23ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።
የኢትዮጵያ ኩራት በሆነው የአየር ኃይል 90ኛ ዓመት የጎዳና ላይ ሩጫ በመሳተፋችን ክብር ይሰማናል- የውድድሩ ተሳታፊዎች
Nov 30, 2025 106
አዲስ አበባ፤ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የአየር ክልል በትጋት በመጠበቅ የኢትዮጵያዊያን ኩራት በሆነው የአየር ኃይል 90ኛ ዓመት የጎዳና ላይ ሩጫ በመሳተፋችን ክብር ይሰማናል ሲሉ የውድድሩ ተሳታፊዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ በዓል በማስመልከት የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በቢሾፍቱ ከተማ ተካሂዷል። የጎዳና ላይ ሩጫው ‟ለአየር ኃይል ዕድገት በሙሉ አቅሜ እሮጣለሁ” በሚል መሪ ቃል ነው የተካሄደው። በመርሀ ግብሩ የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ፣ የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አለማየሁ አሰፋ፣የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች፣የሠራዊት አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ኢዜአ በውድድሩ ተዘዋውሮ ያነጋገራቸው ተሳታፊዎችም የኢትዮጵያ ኩራት በሆነው አየር ኃይል የተመሰረተበትን 90ኛ ዓመት የጎዳና ላይ ሩጫ በመሳተፋቸው ክብር እንደተሰማቸው ተናግረዋል። ከተሳታፊዎቹ መካከል ዮናስ ደበላ አየር ኃይል የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ሰላምና ሉዓላዊነትዊ ደህንነት የጀርባ አጥንት ተቋም መሆኑን ገልጿል። ሌላኛው አስተያየት ሰጭ መሰለ ታዬ በበኩላቸው አየር ኃይል ባለፉት 90 ዓመታት ትልልቅ ታሪክ እና ድል ያስመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያንም ከውጭ እና ከውስጥ ጠላት የታደገ በልፋት እና ትጋት ዛሬ ላይ የደረሰ ተቋም መሆኑን ተናግረዋል። አየር ኃይል እንደ ሀገር ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው ተቋም መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጭ ፍሬዘር አሰግድ ናት። ለመላው የሠራዊቱ አባላትም የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላልፋለች። ሌላኛው አስተያየት ሰጭ ገመዳ ፊዳሞ አየር ኃይል የኢትዮጵያን የአየር ክልል በማስጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድም የበለጸገች ኢትዮጵያን የሚያስተላልፍ መሆኑንም ጠቁመዋል። ጌታ ያውቃል አሸናፊ በበኩሉ የኢትዮጵያ አየር ኃይል የመላው ጥቁር ህዝብ ኩራት የሆነ ተቋም መሆኑን ገልጿል። የኢትዮጵያ አየር ኃይል ለልማት እና ሀገር እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጭ መብሩክ አህመድ ናት።    
ታንዛንያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ አለፈች
Nov 30, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ታንዛንያ ኬንያን 3 ለ 1 አሸንፋለች። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ንሂንጎ ሉዜሌንጋ፣ ሉክማን ምባላሳሉ እና ሶአን ሻባኒ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አርምስትሮንግ ኦሞንዲ ለኬንያ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ታንዛንያ ውጤቱን ተከትሎ ወደ ፍጻሜ አልፋለች። በተጨማሪም እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት ለሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ሴካፋ ዞንን ወክላ ያለፈች የመጀመሪያ ሀገር ሆናለች። ተሸናፊዋ ኬንያ ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ትጫወታለች። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከዩጋንዳ ጋር ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ጨዋታዋን ታደርጋለች። ኢትዮጵያ ካሸነፈች ለአፍሪካ ዋንጫ ታልፋለች። በሴካፋ ዞን ማጣሪያ ከአንድ እስከ ሶስት የሚወጡ ሀገራት ለአፍሪካ ዋንጫ ያልፋሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል አዳማ ከተማን አሸነፈ 
Nov 30, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የዘጠነኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል አዳማ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተካሄደው ጨዋታ ቤተልሄም መንታሎ፣ ትዕግስት ወርቁ እና ጽዮን ፈየራ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። መቻል በ17 ነጥብ አራተኛ ድሉን በማስመዝገብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በሰባት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ10 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በረድኤት አስረሳኸኝ ግቦች ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ19 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በአራት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የዘጠነኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል።
ኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የሚያስችላትን ወሳኝ ጨዋታ ከዩጋንዳ ጋር ታደርጋለች
Nov 30, 2025 137
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ማጣሪያ ከዩጋንዳ አቻው ጋር የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዋን ዛሬ ያደርጋል። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። አዘጋጇ ኢትዮጵያ በምድብ አንድ በ10 ነጥብ መሪ ሆና ማጠናቀቋ ይታወቃል። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ታዳጊ ብሄራዊ ቡድን በምድቡ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በጨዋታዎቹ 10 ግቦችን ሲያስቆጥር 4 ጎሎችን አስተናግዷል።ሰባት ግቦችን ከመረብ ላይ ያሳረፈው ዳዊት ካሳው የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው።   ተጋጣሚዋ ዩጋንዳ በምድብ ሁለት በዘጠኝ ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በብሪያን ሴንዮንዶ የምትመራው ዩጋንዳ በምድቡ ባካሄደቻቸው አራት ጨዋታዎች ሶስቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፋለች። በጨዋታዎቹ ላይ 20 ግቦችን ስታስቆጥር ሁለት ጎሎችን አስተናግዳለች። ኢትዮጵያ ዩጋንዳን ካሸነፈች ለፍጻሜ ከማለፍ ባሸገር እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ማለፏን ታረጋግጣለች። ኢትዮጵያ በጨዋታው ብትሸነፍ፤ በደረጃው ጨዋታ አሸንፋ ሶስተኛ ከወጣች ለአፍሪካ ዋንጫው ታልፋለች። ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1997 ቦትስዋና ባዘጋጀችው ውድድር ላይ ነበር። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ታንዛንያ ከኬንያ ከቀኑ 6 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። ታንዛንያ በምድብ ሁለት በ12 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድቡ ባደረገቻቸው አራት ጨዋታዎች 19 ግቦችን ስታስቆጥር የተቆጠረባት አንድ ግብ ብቻ ነው። ተጋጣሚዋ ኬንያ በምድብ ሁለት በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድቡ አራት ጨዋታዎችን አድርጋ ሁለቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፋለች። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይታለች። አምስት ግቦችን ስታስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዳለች። የግማሽ ፍጻሜ አሸናፊዎቹ ሕዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚደረገው የፍጻሜ ጨዋታ ያልፋሉ። በውድድሩ ላይ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የሚወጡ ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ይሳተፋሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Nov 30, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ ፋሲል ከነማ እና ወላይታ ድቻን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያገናኛል። ፋሲል ከነማ በሊጉ ባደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች አራቱን ሲያሸንፍ በሶስቱ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። ቡድኑ በ15 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ወላይታ ድቻ በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በአራቱ ሽንፈት ሲያስተናግድ ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ስድስት ግቦች ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎችን አስተናግዷል። ወላይታ ድቻ በአምስት ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ፋሲል ከነማ ጨዋታውን ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና ይረከባል። በአንጻሩ ወላይታ ድቻ ድል ከቀናው ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። በሌላኛው መርሃ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።   ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ድል አላስመዘገበም። ስድስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 13 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታም በሊጉ እስከ አሁን ያሸነፈው ጨዋታ የለም። ሶስት ጊዜ ሽንፈት ሲገጥመው በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ስምንት ግቦችን በሰባቱ ጨዋታዎች ሲያስቆጥር 12 ጎሎችን አስተናግዷል። መቀሌ 70 እንደርታ በአራት ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች የመጀመሪያ ሶስት ነጥባቸውን ለማግኘት ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ ከኢትዮጵያ መድን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሊጉ ካደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ያሸነፈው ባህር ዳር ከተማ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አጋጥሞታል። ሶስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ሰባት ግቦችን ሲያገባ ስድስት ጎሎችን አስተናግዷል። ባህር ዳር ከተማ በዘጠኝ ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በውድድር ዓመቱ ስድስት ጨዋታዎችን አድርጎ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አጋጥሞታል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ አምስት ጎሎችን አስተናግዷል። መድን ቀሪ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በስምንት ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከአዳማ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ ካካሄዳቸው ሰባት ጨዋታዎች መካከል አራቱን ሲያሸንፍ በአንዱ ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ14 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ በበኩሉ ከሰቤት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በእነዚህ ጨዋታዎች ላይ አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦች ተቆጥረውበታል። አዳማ ከተማ በ12 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የስምንተኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ሕዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና ሊጉን በ16 ነጥብ እየመራ ነው። ወላይታ ድቻ፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ አርባምንጭ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ17ኛ እስከ 20ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም