ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ ነው
Nov 12, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር በትብብር የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑን በተለያዩ ሀገራት የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ገለፁ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን መግለፁ ይታወቃል። ሚኒስቴሩ በመግለጫው ባለፉት አራት ዓመታት በመካከለኛ ምስራቅ፣አፍሪካ፣ ማይናማር እና የእስያ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ከ500 ሺህ በላይ ዜጎች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ማድረግ መቻሉን ጠቁሟል። በዚምባብዌ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደርና በሞሪሽየስ፣ በዛምቢያ፣ በምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) የኢትዮጵያ ተጠሪ ረሺድ መሀመድ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የውጭ ዲፕሎማሲ ከሚያተኩርባቸው ጉዳዮች አንዱ የዜጎችን ክብርና መብት ማስጠበቅ ነው። ኤምባሲዎቹ ዜጎች ችግር ሲገጥማቸው የመከታተልና የመፍታት ስራዎችን ሲያከናውን መቆየታቸውንና ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ዜጎችን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ወደ ሀገራቸው ለመመለስ እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል። ባለፈው ዓመት አንድ ሺህ የሚጠጉ ዜጎችን ወደ ሀገር ቤት መመለስ መቻሉን ጠቅሰው፤ ኤምባሲው ፓስፖርት የማደስ፣ መረጃ የማረጋገጥና ተያያዠ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። በባህሬን የኢፌዴሪ ቆንስላ ጄኔራል ጽህፈት ቤት ቆንስል ጄኔራል አምባሳደር ሽፈራው ገነቲ፤ ሁለቱ ሀገራት የስራ ስምሪት ስምምነት ባይኖራቸውም የዜጎች ክብርና ጥቅም እንዲከበር ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተሰራ ነው ብለዋል። በዚህም በተለያየ ምክንያት ለእስር የተዳረጉ ዜጎች ነፃ የህግ አገልግሎት እንዲያገኙና ዜጎች በህጋዊ መንገድ እንዲንቀሳቀሱና በነጻነት እንዲሰሩ አስፈላጊውን ሁሉ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ጽህፈት ቤቱ ባደረገው ጥረት ባለፈው ዓመት ከስድስት ሺህ በላይ ዜጎች ህጋዊ መኖሪያ ፈቃድ እንዲያገኙ ማስቻሉን አንስተው፤ ወደ ሀገራቸው መመለስ የሚፈልጉ 291 ዜጎችን እንዲመለሱ መደረጉንም ገልፀዋል። በዱባይና ሰሜን ኤምሬትስ የኢፌዴሪ ቆንስላ ጄኔራል ፅህፈት ቤት ተጠባባቂ ጉዳይ ፈፃሚ አስመላሽ በቀለ በበኩላቸው፤ የዜጎችን መብትና ጥቅም ለማስከበር የተለያዩ ተግባራትን እያከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዚህም ፅህፈት ቤቱ ባለፉት ሁለት ዓመታት የፓስፖርት እድሳት፣ የውክልና እና የዳያስፖራ አገልግሎቱን በኦንላይን እየሰጠ መሆኑን ገልፀዋል። ዜጎች ከስራ ውል ጋር የተያያዙ ችግሮች ሲገጥማቸው መብታቸውን ለማስከበር ከኢትዮጵያ ኮሙዩኒቲ ማህበር ጋር በመተባበር እየተሰራ ነው ብለዋል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ፤ ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመከላከል ብሄራዊ ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ከስደት ተመላሾች በሀገር ውስጥ የስራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑና በህገወጥ የሰዎች ዝውውር ላይ የሚሳተፉ ደላሎች በህግ እንዲጠየቁ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። ሚኒስቴሩ ከስራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ዜጎች ደህንነቱ በተጠበቀ ህጋዊ መንገድ እንዲጓዙ ግንዛቤ የማስጨበጥና ለተመላሾች የማህበራዊ አገልግሎትና የአገር ውስጥ የስራ እድል ፈጠራ ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑንም አመላክተዋል። የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍፁም አረጋ መንግስት ከተለያዩ ሀገራት ጋር ምክክር በማድረግና ስምምነት በመፈጸም የዜጎችን መብት ለማስጠበቅ እየሰራ ነው ብለዋል። በተለያዩ ሀገራት የሚገኙ ኤምባሲዎች የኢትዮጵያ ኮሙዩኒቲ ማህበሮችን በማደራጀት ዜጎች የሚገጥማቸውን ችግር ለመፍታት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
ዜጎች አስከፊነቱን ተገንዝበው መደበኛ ካልሆነ ፍልሰት ሊቆጠቡ ይገባል
Nov 12, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 3/2018(ኢዜአ)፡- በመንግሥት ደረጃ ብሎም ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት የሚያከናውነው መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን የመከላከልና መቆጣጠር ሥራ እንደተጠበቀ ሆኖ ዜጎች ከድርጊቱ እራሳቸውን ማቀብ እንዳለባቸው ተገለጸ። በሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር መከላከልና ከፍልሰት ተመላሽ ዜጎች ድጋፍና ክትትል መሪ ሥራ አስፈፃሚ ደረጀ ተግይበሉ እንዳሉት፤ መደበኛ ባልሆነ ፍልሰት ወደ ተለያዩ ሀገራት የሄዱና ለችግር የተጋለጡ ዜጎችን የመመለስ ሥራ እየተከናወነ ነው። ወደ ሀገራቸው ከተመለሱ በኋላ ተገቢው የሥነ-ልቦናና ማኅበራዊ ድጋፍ እንዲያገኙ ተደርጎ ከቤተሰብ እና ከማኅበረሰቡ ጋር መቀላቀላቸውን ጠቅሰዋል። በክልሎች የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮዎች እና በሥራና ክኅሎት ቢሮዎች አማካኝነት ተገቢውን ስልጠና ወስደው የማቋቋም ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አረጋግጠዋል። በመንግሥት በኩል ተገቢው ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸው፤ በግላቸው ለመንቀሳቀስ የፈለጉም በራሳቸው ጥሪት የግል ሥራቸውን እየሠሩ መሆኑን አመላክተዋል። በሀገር ውስጥ ያሉ የሥራ አማራጮችን ማስተዋል እና ወደ ውጭ መሄድ ሲያስፈልግም በሕጋዊ መንገድ ብቻ እንዲሆን መክረው፤ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት ዘርፈ-ብዙ ጉዳት እንደሚስከትል አስገንዝበዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቋል። ባለፉት አራት ዓመታትም በተለያዩ የመካከለኛ ምሥራቅ፣ የአፍሪካ እና እንደ ማይናማር ያሉ የእስያ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ከ500 ሺህ በላይ ዜጎችን ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ማድረግ መቻሉን አስታውቋል።
የአፍሪካ የመንገድ ደህንነት ቀን በአዲስ አበባ ይከበራል
Nov 12, 2025 106
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ የመንገድ ደህንነት ቀን ህዳር 7 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ አድዋ ድል መታሰቢያ ይከበራል። የመንገድ ደህንነት ቀን ሁነት በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ስር በሚገኘው የአፍሪካ የመንገድ ደህንነት ኢኒሼቲቭ፣ የኢፌዴሪ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር፣ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት እና የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን(ኢሲኤ) የጋራ ትብብር የተዘጋጀ ነው። የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ 2012 ባሳለፈው ውሳኔ መሰረት ቀኑ በየዓመቱ የሚከበር ሲሆን ከዓለም የትራፊክ አደጋ ተጎጂዎች መታሰቢያ ቀን ጋር የተሳሰረ መሆኑም ተመላክቷል። ቀኑ በትራፊክ አደጋ ምክንያት ህይወታቸውን ያጡ እና የተጎዱ ሰዎች የሚታሰቡበትና በአፍሪካ ደረጃ የመንገድ ደህንነትንና ዘላቂ የትራንስፖርት እንቅስቃሴን ለማረጋገጥ ሀገራት የጋራ ቁርጠኝነታቸውን የሚገልጹበት ነው። አፍሪካ ከፍተኛ የትራፊክ አደጋዎችን ከሚያስተናግዱ አህጉራት መካከል አንዷ መሆኗን የአፍሪካ ህብረት ገልጿል። ከዓለም ተሽከርካሪዎች ውስጥ ከአራት በመቶ በታች የሚገኝባት አፍሪካ የዓለም 25 በመቶ ገደማ የትራፊክ አደጋ ሞት እንደሚመዘገብባት አመልክቷል። ከሚጎዱት መንገደኞች፣ የሳይክል እና ሞተር አሽከርካሪዎች መካከል አብዛኞቹ ወጣቶች መሆናቸውን ገልጾ የህብረቱ አባል ሀገራት በትራፊክ አደጋዎች ምክንያት ሁለት በመቶ የሚሆን ዓመታዊ ጥቅል ምርታቸው (ጂዲፒ) ወጪ እንደሚያደርጉ ነው ሀብረቱ ያስታወቀው። ቀኑ በአፍሪካ የመንገድ ደህንነት የድርጊት መርሃ ግብር (ከእ.አ.አ 2021 እስከ 2030 የሚቆይ) ጥላ ስር የተቀናጀ የተግባር ምላሽ እና አጋርነትን የማጠናከር ግብ እንዳለውም ተመላክቷል። በመንገድ ደህንነት ቀን የትራፊክ አደጋ ተጎጂዎች የሚታወሱ ሲሆን ሀገራት እ.አ.አ በ2030 የትራፊክ አደጋ ሞትን በ50 በመቶ ለመቀነስ የገቡትን ቃል ለማደስ የፖለቲካ ቁርጠኝነታቸውን ይገልጻሉ ተብሎ ይጠበቃል። የአፍሪካ የመንገድ ደህንነት ኢኒሼቲቭ በመረጃ ላይ የተመሰረተ የቁጥጥር ስርዓት ማጠናከርና በህብረቱ አባል ሀገራት “Safe System” የተሰኘ ዘመናዊ የመንገድ ደህንነት ስርዓት ማዕቀፍ የማስተዋወቅ ስራ እንደሚከናወንም ነው ህብረቱ ያስታወቀው።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ስብዕና መገንቢያ ማዕከላትን ቁጥር ለማሳደግ እየተሰራ ነው
Nov 11, 2025 146
ጂንካ ፤ ሕዳር 2/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ስብዕና መገንቢያ ማዕከላትን ቁጥር ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ወጣቶች ጉዳይና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ኮሚሽን ገለጸ። በክልሉ የአፍላ ወጣቶችና ወጣቶች የአቅም ማጎልበቻ የንቅናቄ መድረክ በጂንካ ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ የክልሉ ወጣቶች ጉዳይና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ኮሚሽን ኮሚሽነር ማርቆስ ማቲዮስ እንዳሉት ፤ አሻግሮ የሚያይና በሚዛናዊ አስተሳሰብ የተገነባ ትውልድ ማብዛት ያስፈልጋል። አሁን ላይ በክልሉ 512 የስብዕና መገንቢያ ማዕከላት መኖራቸውን ጠቅሰው፤ በቀጣይም የወጣቶች ሁለንተናዊ ስብዕና መገንቢያ ማዕከላትን ለማበራከት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ወጣቶች በሀገራዊ ጉዳዮች ንቁ ተሳትፎ የሚያደርጉበትና ልምድ የሚለዋወጡበት አውድም ይመቻቻል ብለዋል። በመድረኩ ላይ የኮሚሽኑ ተጠሪ ተቋማት፣የወጣት ተወካዮችና በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ተገኝተዋል ።
የታሪክ ተመራማሪና መምህር ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ ስርዓተ ቀብር ተፈጸመ
Nov 11, 2025 153
አዲስ አበባ፤ ህዳር 2/2018(ኢዜአ)፦የታዋቂው የታሪክ ተመራማሪና መምህር ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ የቀብር ስነ ስርዓት ዛሬ በጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ-ክርስቲያን ተፈጽሟል። በቀብር ስነ ስርአቱ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ሃላፊዎች ፣የፕሮፌሰር ላጲሶ ቤተሰቦች እና ወዳጅ ዘመዶች ተገኝተዋል። በቀድሞው በከንባታ እና ሐዲያ አውራጃ በኩፋላ ሐበሌ ግንቦት 12 ቀን 1930 ዓ.ም የተወለዱት ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በቢቾ ሆሳዕና ሚሽን ትምህርት ቤት ፣የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ አዳማ በሚገኘው የአፄ ገላውዴዎስ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና ባይብል አካዳሚ ተከታትለዋል። በፍልስፍና እና በታሪክ ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ዶክትሬት ዲግሪ ድረስ ትምህርታቸውን በአሜሪካን ሀገር ተከታትለዋል። በኋላም የፕሮፌሰርነት ማዕረግ አግኝተው፤ለሁለት ዓመታት በቨርጂኒያ ዩንየን ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ሲያስተምሩ ቆይተዋል። የ1966 ዓ.ም የኢትዮጵያ አብዮት ተከትሎ ወደ ሀገራቸው ተመልሰው፤ በታሪክ ምርምር እና በማስተማር አገራቸውን አገልግለዋል። በኢትዮጵያ ታሪክ ጥናት የራሳቸውን አሻራ ያሳረፉት ፕሮፌሰሩ ለኢትዮጵያ ታሪክ እድገት አስተዋጽኦ ያበረከቱ መጻሕፍትን አበርክተዋል። የኢትዮጵያ ረጅም የሕዝብና የመንግሥት ታሪክ ፣.የኢትዮጵያዊነት ታሪካዊ መሰረቶችና መሳሪያዎች ፣የቀይ ባሕርና የዓባይ ሸለቆ ሚና እንዲሁም አጭር የጌዴኦ ህዝብ ታሪክን ጨምሮ በርካታ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ያተኮሩ መጻሕፍትን ጽፈዋል። ህብረ ብሄራዊ አንድነት እንዲጎለብት የሚያግዙ በርካታ የምርምር ሥራዎችንም አከናውነዋል። የታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ ባለትዳር እና የሦስት ሴት ልጆች አባት የነበሩ ሲሆን፤ ባደረባቸው ህመም በህክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ87 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል።
የታሪክ ተመራማሪው ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ ፕሮፌሰር በኢትዮጵያ የታሪክ አቀራረብ ሥልት ውስጥ የጋራ ትርክት በመገንባት ዘመን ተሻጋሪ አሻራ አሳርፈዋል
Nov 11, 2025 121
አዲስ አበባ፤ሕዳር 2/2018 (ኢዜአ)፡-የታሪክ ተመራማሪው ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) በኢትዮጵያ የታሪክ አቀራረብ ሥልት ውስጥ የጋራ ትርክት በመገንባት ዘመን ተሻጋሪ አሻራ ማሳረፋቸውን የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ ገለጹ። የታሪክ ተመራማሪው ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) የአስከሬን ሽኝት ሥነ -ሥርዓት ተካሂዷል። በሽኝት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ እና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ፣ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጂጌ (ዶ/ር)፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር)፣ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች፣የሀይማኖት አባቶችን ጨምሮ የፕሮፌሰሩ የሥራ ባልደረቦችና ወዳጅ ዘመዶች ተገኝተዋል። በዚሁ ወቅት ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) በኢትዮጵያ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ የጋራ ትርክትን ለመገንባት የበኩላቸውን ጥረት ማድረጋቸው ተገልጿል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ ፕሮፌሰር ላጲሶ በአካታች የታሪክ አዘጋገብ በአካዳሚው ዘርፍ ብርቱ ትጋት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። የተዛባ የታሪክ ገጽን በማረቅ የጋራ ትርክት መገንባት ላይ አሻራቸውን ማሳረፋቸውንም ነው የገለጹት። ፕሮፌሰሩ ከሀገራቸው ባለፈ በጥቁር አፍሪካውያን የታሪክ ምልከታ ላይ አስተዋጽኦ ነበራቸው ብለዋል። የጋራ ትርክትን ለመገንባት ያደረጉት ጥረት ሀገር ወዳድነታቸውን ያሳያል ብለዋል። ቢጻፍም ባይጻፍም ሁሉም የራሱ ታሪክ አለው በሚል አቋማቸው የሚታወቁት ፕሮፌሰሩ፤ በኢትዮጵያ የታሪክ አጻጻፍ ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን ለማረም ጥልቅ ጥናትና ምርምር ማድረጋቸውም ተናግረዋል።
የታሪክ ተመራማሪው ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) የአስከሬን ሽኝት ሥነ -ሥርዓት እየተካሄደ ነው
Nov 11, 2025 130
አዲስ አበባ፤ሕዳር 2/2018 (ኢዜአ)፡-የላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) አስከሬን ሽኝት መርሐ ግብር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 6 ኪሎ ካምፓስ እየተካሄደ ነው፡፡ በሽኝት ሥነ-ሥርዓቱ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች የፕሮፌሰሩ የሥራ ባልደረቦችና ወዳጅ ዘመዶች ተገኝተዋል። የታሪክ ተመራማሪው ላጲሶ ጌ’ዴሌቦ (ፕ/ር) ባደረባቸው ሕመም ሕክምናቸውን ሲከታተሉ ቆይተው ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው ይታወቃል፡፡ ፕሮፌሰር ላጲሶ በኢትዮጵያና በአፍሪካ የታሪክ ጥናትና ምርምር በማካሄድ የተለያዩ የታሪክ መጽሐፍትን ለአንባቢያን በማበርከት አገራቸውን አገልግለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የሴቶችን የገቢ አቅም ለማሻሻል የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Nov 11, 2025 89
አምቦ፣ህዳር 2/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል የሴቶችን የገቢ አቅም ለማሻሻል የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ቢሮ ገለፀ። የኦሮሚያ ክልል ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ቢሮ በምዕራብ ሸዋ ዞን ኤጀሬ ወረዳ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ለአቅመ ደካሞች የተገነቡ መኖሪያ ቤቶችን አስረክቧል። በዚሁ ጊዜ የክልሉ ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ መብራት ባጫ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሴቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው። በተለይም አቅም የሌላቸው እና የቤተሰብ ሀላፊ የሆኑ ሴቶች ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማሳደግ እንዲችሉ የተለያዩ አካላትን በማስተባበር ድጋፍ እየተደረገ ነው ብለዋል። ባለፈው የክረምት ወራት የተጀመሩ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታ በዚህ ወቅት ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች እየተላለፈ መሆኑን ጠቅሰው ቀሪዎቹንም አጠናቆ ለማስረከብ የሚደረገው ርብርብ ይቀጥላል ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን ሴቶች በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ስራዎች እንዲሰማሩ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም በርካታ ሴቶች በወተት ላም እርባታ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በዶሮ እርባታ እና በሌሎች የስራ ዘርፎች ተሰማርተዋል ብለዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ሰቶችና ህፃናትና ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ክብቱ ድሪባ በበኩላቸው፣ በዞኑ የሴቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎች ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ በክረምት ወራት የተጀመሩ የአቅመ ዳካማ ሴቶች ቤት ግንባታ ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች እየተሰጠ መሆኑን ተናግረው በትናንትናው እለትም ሁለት መኖሪያ ቤቶች መተላለፋቸውን ገልጸዋል። ከዚህ ጎን ለጎን በኤጀሬ ወረዳ አቅመ ደካማ ሴቶች ተደራጅተው በወተት ላሞች እርባታ መሰማራታቸውን ገልጸው ተጠቃሚነታቸውም እያደገ መምጣቱን አመልክተዋል። በበጎ ፈቃድ አገልግሎት መኖሪያ ቤት የተገነባላቸው ወይዘሮ ብርቄ ዳባ፣ የገንዘብ አቅም ስለሌላቸው ሊፈርስ የተቃረበ ቤት ውስጥ በአስቸጋሪ ሁኔታ ይኖሩ እንደነበረ አስታውሰዋል። አሁን በተገነባላቸው አዲስ መኖሪያ ቤት ችግራቸው የሚቀርፍላቸው በመሆኑ መደሰታቸውን ገልጸው በጎ ፈቃደኞችንም አመስግነዋል። በሌላ በኩል በማህበር ተደራጅተው ስራ ከጀመሩ ሴቶች መካከል ወይዘሮ ባይሴ ቱሉ እንዳሉት፣ በተሰማሩበት የወተት ላም እርባታ የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን እንደሚተጉ ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የምታቅደውን ብልጽግና እውን ማድረግ የሚችሉ ብቁ ዜጎችን ለማፍራት ለትምህርት ጥራት ትኩረት ተሰጥቷል
Nov 11, 2025 94
አዳማ፤ህዳር 2/2018( ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የምታቅደውን ብልጽግና እውን ማድረግ የሚችሉ ብቁ ዜጎችን ለማፍራት ለትምህርት ጥራት ትኩረት መሰጠቱን የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተናገሩ። 34ኛው ሀገር አቀፍ የትምህርት ጉባዔ “ፍትሃዊና ጥራት ያለው ትምህርት ለሁሉም” በሚል መሪ ሀሳብ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ይገኛል። በጉባዔው መክፈቻ ንግግር ያደረጉት የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ፣ የትምህርት ዘርፉ ውጤታማ ዜጎችን ማፍራት እንዲችል መግባባት ተፈጥሮ ጥራትን ለማረጋገጥ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በትምህርት ዘርፉ ያሉትን ማነቆዎች በመፍታት ይበልጥ ውጤታማ ለመሆን የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ከሁሉም በላይ ኢትዮጵያ የምታቅደውን ብልጽግና እውን ማድረግ የሚችሉ ብቁ ዜጎችን ለማፍራት ለትምህርት ጥራት ትኩረት ተሰጥቶ በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ጉባዔውም በትምህርት ዘርፉ ታቅደው የተሰሩ ስራዎችን በጋራ ለመገምገምና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ የጋራ መግባባት ለመፍጠር ያለመ መሆኑን አስታውቀዋል። በጉባዔው የትምህርት ሴክተሩን ለማሳካት የተያዙ ግቦች ዙሪያ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የጠራ አመለካከት በመያዝ ይበልጥ መረባረብ እንደሚገባቸው ለማስገንዘብ መሆኑን አንስተዋል። የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ ሃላፊ ቶላ በሪሶ (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በክልሉ የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ላይ ትኩረት በመስጠት ለትምህርት ጥራት መሰረት መጣሉን አንስተዋል። የተማሪዎች መጠነ ማቋረጥ እና ሌሎችንም ችግሮች ለመፍታት ሁላችንም በሚገባን ልክ ተሰናስለን የትምህርት ሥርዓቱን መምራት ይኖርብናል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። በጉባዔው ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣የክልል ትምህርት ቢሮ አመራሮች፣ የዩኒቨርሲቲ አመራሮች፣ ጥሪ የተደረገላቸው ባለድርሻ እና አጋር አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሮግራሞች ክለሳ በዚህ ዓመት ወደ ዩኒቨርሲቲ በገቡ ተማሪዎች ላይ ተግባራዊ መደረግ ይጀምራል
Nov 11, 2025 237
አዲስ አበባ፤ሕዳር 2/2018 (ኢዜአ)፡-የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተጀመረው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሮግራሞች ክለሳ በዚህ ዓመት ወደ ዩኒቨርስቲ በሚገቡ ተማሪዎች ላይ ተግባራዊ እንደሚደረግ የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ በ2018ዓ.ም አዳዲስ ከ80 በላይ የከፍተኛ ትምህርት ፕሮግራሞች እንደሚከለሱ ተመላክቷል፡፡ የትምህርት ሚኒስቴር የአካዳሚክ ጉዳዮች መሪ ስራ አስፈጻሚ ኤባ ሚጀና (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ መንግስት የትምህርት ጥራትን እና አግባብነት ለማረጋገጥ ከሚሰራቸው ስራዎች መካከል የከፍተኛ ስርዓተ ትምህርት ፕሮግራሞች ክለሳ ይገኝበታል። የፕሮግራሞች ክለሳ ዓለም አቀፍ የትምህርት ስታንዳርዶችን የጠበቀ የትምህርት ጥራት አግባብነትን በማረጋገጥ የሀገሪቱን የልማት አቅጣጫዎች የሚደግፍ መሆኑን አንስተዋል። ቀደም ሲል የነበረው ሥርዓተ ትምህርት በንድፈ ሀሳብ ላይ ያተኮረ መሆኑን የተናገሩት መሪ ስራ አስፈጻሚው፤ አሁን ያለው ክለሳ ግን ተማሪዎች ተወዳዳሪ የሚያደርግ ተግባር ተኮር እንዲሆን መደረጉን ተናግረዋል። የከፍተኛ ትምህርት ፕሮግራሞች ክለሳ በዘመናዊው ዓለም አቀፍ የሥራ ገበያ የሚፈለጉትን ክህሎቶች፣ ችግር ፈቺነት፣ ፈጠራ፣ እና ሙያዊ ስነምግባርን ያካተተ መሆኑን አስታውቀዋል። ክለሳው የሀገር በቀል እውቀትን በማካተት የትምህርት ተቋማቱን ልዩ ከማድረጉም በላይ ተመራቂዎች በየትኛውም የዓለም ክፍል እንዲማሩና እንዲሰሩ የሚያደርግ መሆኑን አመልክተዋል። መሪ ስራ አስፈጻሚ ኤባ ሚጀና (ዶ/ር) በሀገረቱ በመጀመሪያ ዲግሪ 314 ፕሮግራሞቸ መኖራቸውን አንስተው፤ በቀጣይ ሁሉም የትምህርት ፕሮግራሞች ላይ ክለሳ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እስካሁን አምሳ አምስት ፕሮግራሞች መከለሳቸውን ጠቁመው፤ 2018ዓም ሰማንያ አዳዲስ ፕሮግራሞችን በመከለስ በአጠቃላይ ከ100 በላይ ለማድረስ መታቀዱን አስታውቀዋል፡፡ ሚኒስቴሩ የትምህርት ፕሮግራሞቹ ክለሳ ቴክኖሎጂን መሰረት በማድረግ መዘጋጀቱን ገልጸው፤ ክለሳው ወደ ስራ ሲገባ መምህራን አዲሱን ይዘትና የአተገባበር ዘዴ ለመረዳት የሚያስችላቸው ሙያዊ ሥልጠና እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የፕሮግራሙ ክለሳ በዚህ ዓመት ወደ ዩኒቨርሲቲ በገቡ ተማሪዎች ላይ ተግባራዊ የሚደረግ ሲሆኑ በመሰረታዊነት የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ በኩል ትልቅ ሚና እንደሚኖረው አስታውቀዋል፡፡ የክለሳው ዓላማ ውጤታማ እንዲሆን የዩኒቨርሲቲዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ትብብር ወሳኝ መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል።
የፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ የቀብር ስነስርዓት ነገ ይፈጸማል
Nov 10, 2025 167
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ የፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ ስርዓተ ቀብር ነገ ይፈጸማል። ኢዜአ ከቤተሰባቸው ያገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ነገ 5:00 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስድስት ኪሎ ካምፓስ የአስከሬን ሽኝት ይከናወናል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ደግሞ የቀብር ስነስርዓቱ በጴጥሮስ ጳውሎስ ቤተክርስቲያን እንደሚፈጸም ተገልጿል። ፕሮፌሰር ላጲሶ በህይወት በነበሩበት ዘመን ለሀገራቸው ኢትዮጵያ እንዲሁም ለአፍሪካ የታሪክ ጥናትና ምርምር ትልቅ አበርክቶ የነበራቸው ሲሆን፤ የተለያዩ የታሪክ መፅሀፍቶችን ፅፈው ያሳተሙና በዘርፉ አንቱታን ያገኙ ታላቅ ምሁርም ነበሩ። ፕሮፌሰር ላጲሶ የኢትዮጵያውያንን የጋራ እሴት፣ ባሕልና ቋንቋ በማውሳት የሕዝቦች ታሪክ ጎልቶ እንዲታወቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውም ተመላክቷል፡፡ ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ.ዴሌቦ ባጋጠማቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በትናንትናው ዕለት ነበር ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ።
አፍሪካ የሰብዓዊ ድጋፎችን በራሷ አቅም ለማቅረብ የጀመረችውን ጥረት አጠናክራ መቀጠል ይኖርባታል
Nov 10, 2025 146
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ የሰብዓዊ ድጋፎችን በራሷ አቅም ለማቅረብ የጀመረችውን ጥረት አጠናክራ መቀጠል እንደሚኖርባት ተገለጸ። በአፍሪካ ህብረት የስደት፣ ስደተኞች እና የውስጥ ተፈናቃይ ሰዎች የልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ አምስተኛ መደበኛ ስብሰባ መካሄድ ጀምሯል። በዚሁ ወቅት የስደተኞችና ተፈናቃዮችን ችግሮች ለመፍታት የጋራ ቁርጠኝነት፣ ትብብርና የአገር ውስጥ መፍትሔዎች ወሳኝ መሆናቸው ተጠቁሟል። ስብሰባው በአጀንዳ 2063 አቅጣጫዎች መሠረት የስደት፣ የስደተኞች እና ተፈናቃዮች ጉዳዮች ላይ የሚተገበሩ ፖሊሲዎችን እና ስትራቴጂዎችን ለማረጋገጥ ያለመ ነው። በስብሰባው የአፍሪካ ባለሙያዎች ስደትን፣ መፈናቀልን እና ሰብዓዊ ፈተናዎችን በትብብር እና በአገር ውስጥ መፍትሔዎች ለመፍታት የጋራ ቁርጠኝነታቸውን አረጋግጠዋል። ባለሙያዎቹ በአህጉሪቱ ያለውን በስደት እና በመፈናቀል ምክንያት የሚመጡ ሰብዓዊ ፈተናዎችን ለማቃለል አንድነትና ቀጣይነት ያለው አቅጣጫ እንዲኖር ጥሪ አቅርበዋል። የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን፣ የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግሥታት የኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለአፍሪካ ወኪል ሄርቭ ኩአቴ በዚሁ ወቅት፣ ስብሰባው ቁርጠኝነትን ወደ ተግባር ለመለወጥ እና ስደተኞችን የሚጠቅሙ ፖሊሲዎችን ለመመልከት ያለመ ነው ብለዋል። ይህም አፍሪካ ለዘላቂ ልማት ያላትን ራዕይ ከፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። በአህጉሪቷ ለጠንካራና ወጥ ለሆነ ዓለም አቀፍ የስደት አስተዳደር ውጤታማ ምላሽ ለመስጠት ብዝሃነትና ትብብር አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። የዛምቢያ ሪፐብሊክ የኢሚግሬሽን መምሪያ ምክትል ዋና ዳይሬክተር እና የኮሚቴው የቀድሞ ሊቀ-መንበር ኢኖስ ቺቦምቤ በበኩላቸው፤ አሁን ያሉትን ፈተናዎች ለመፍታት በአፍሪካ የሚመሩ የሰብዓዊ ድጋፍ ምላሾች ያስፈልጋል ብለዋል። ሰብዓዊ ድጋፎች ለረጅም ጊዜ በውጫዊ ሀብቶች እና ተዋናዮች ላይ ጥገኛ እንደነበሩ አንስተው፤ ይህን መፍታትና ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለማቅረብ መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል። አፍሪካዊ ተግዳሮቶችን በአፍሪካዊ መፍትሔዎች መፍታት ይገባል ያሉት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ የሰብዓዊ ድጋፎችን በራስ አቅም የማቅረብ ጥረቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም ተናግረዋል። ኮሚቴው በበርካታ ወሳኝ ፖሊሲዎች በመወያየት የስደት፣ የስደተኞች እና የተፈናቀሉ ሰዎችን ከአጀንዳ 2063 ጋር በማጣጣም የሰብዓዊ ማዕቀፎችንና ስልቶችን ማጽደቅ እንዲሁም መደገፍ ላይ ትኩረት እንደሚያደርግም ተጠቁሟል።
የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር በባህል፣ በስፖርት እና ኪነ-ጥበብ ልማት ዘርፍ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን ማጠናከር አለበት
Nov 10, 2025 105
አዲስ አበባ፤ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር በባህል፣ በስፖርት እና ኪነ ጥበብ ልማት ዘርፍ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው የባህልና ስፖርት ሚኒስቴርን የ2018 በጀት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት እቅድ አፈጻጸምን ገምግሟል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ የሩብ ዓመቱን አፈጻጸም ሲያቀርቡ እንዳሉት፤ባለፉት ሶስት ወራት በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በ2018 በጀት ዓመት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን የሚያጠናክሩ እና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸውን በርካታ ኃይማኖታዊ እና ባህላዊ በዓላትን የማስተባበር ሥራ ማከናወኑን አመልክተዋል፡፡ የኪነ ጥበብ ዘርፍን በአግባቡ ለመመራት የኪነ-ጥበብ እና የሥነ-ጥበብ ፈጠራ ልማት የፖሊሲ፣ ደንብ እና መመሪያ ረቂቅ ሰነድ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ በቅርቡም ስራ ላይ እንደሚውል ገልጸዋል። በስፖርት ዘርፍም ተተኪ ስፖርኞችን ለማፍራት የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት ማስመዝገባቸውን ነው የተናገሩት፡፡ በአሁኑ ወቅት የ2029 የአፍሪካ ዋንጫን ማስተናገድ የሚያስችሉ ልዩ ልዩ የስፖርት ማስፋፊያ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑም ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም በቋሚ ኮሚቴው የተሰጡ ግብረ-መልሶችን መሰረት በማድረግ የባህል፣ የስፖርት እና ኪነ-ጥበብ ዘርፉን ለማሳደግ ከመቼውም ጊዜ በላይ በትኩረት እንደሚሰራ አጽንኦት ሰጥተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና የስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ታደለ ቡራቃ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ሚኒስቴሩ ያከናወናቸው ባህልን የማስተዋወቅ፣ የስፖርት ተሳትፎን የማሳደግ እና የኪነ ጥበብ ዘርፉን የማበረታታት ተግባራት በጠንካራ ጎን የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል፡፡ ባህል፣ ስፖርት እና ኪነ-ጥበብ ለቱሪስት መስህብነትና ለገጽታ ግንባታ ካላቸው ፋይዳ ባሻገር የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ ማህበራዊ ትስስርን በማጠናከርና የሀገርን ገጽታ በመገንባት ረገድ ወሳኝ ሚና እንዳላቸውም አመልክተዋል። በቀጣይም ሚኒስቴሩ ወጣቶችን በስፋት ተጠቃሚ በሚያደርጉ የባህል፣ የስፖርትና የኪነ ጥበብ ልማት ሥራዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እንዲሰራ አሳስበዋል። ቋሚ ኮሚቴው ለዘርፉ እድገት አስፈላጊውን ክትትል እና ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል፡፡
ሚኒስቴሩ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያከናወናቸው ያሉ የበጎ ፈቃድ ተግባራትን ማጠናከር አለበት
Nov 10, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያከናወናቸው ያሉ የበጎ ፈቃድ ተግባራትን ማጠናከር እንዳለበት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስገነዘበ፡፡ ቋሚ ኮሚቴው የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርን የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምን ገምግሟል። የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) ባቀረቡት ሪፖርት፣ ሚኒስቴሩ ተቋማዊ የማስፈፀም አቅምን የሚያሳድጉ ተግባራትን ማከናወኑን ገልጸዋል። በሩብ ዓመቱ 25 ሚሊዮን ወጣቶች በበጎ ፈቃድ አገልግሎት መሰማራታቸውን ጠቁመው፤ ከ55 ሚሊዮን በላይ የማኅበረሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመዋል። የሴቶች፣ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያን፣ ውሎና አዳራቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉ ዜጎችን መብትና ደህንነት የሚያስጠብቁ ሥራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሴቶችንና ወጣቶችን ለአመራርነት የሚያበቁ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል፡፡ ቋሚ ኮሚቴው በበኩሉ ሚኒስቴሩ የሕፃናት ጉልበት ብዝበዛን ለመቀነስ፣ የአካል ጉዳተኞችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች እንዲብራሩ ጠይቋል፡፡ ጾታዊ ጥቃትን ለመቀነስ እንዲሁም ሕገ-ወጥ ፍልሰትን ለመከላከል ሚኒስቴሩ እያከናወነ ያለውን ሥራ በተመለከተ ማብራሪያ ጠይቋል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) ከቋሚ ኮሚቴው ለቀረበው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ እንዳሉት በቋሚ ኮሚቴው የሚደረገው ክትትልና ድጋፍ ስራዎችን በጥልቀት ለመስራት አቅም የሚሆን ነው። ፆታዊ ጥቃት እየቀነሰ መሆኑን የሚያሳዩ የተለያዩ ጥናቶች መኖራቸውን አንስተው፤ በሚፈለገው ልክ ለማከናወን ከሚመለከታቸው ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። በህፃናት ጉልበት ብዝበዛና የአካል ጉዳተኞችን የስራ እድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ስራዎች መከናወናቸውንና ስራውን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ቅንጅትና ትብብር ይጠናከራል ብለዋል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ በበኩላቸው፤ ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመከላከል በግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ዜጎች ደህንነቱ የተጠበቀ መንገድ እንዲከተሉ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ህብረተሰቡ በህገ-ወጥ ተግባር የተሰማሩ ደላሎችን እንዲጠቁም እየተሰራ ነውም ብለዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ታደለ ቡራቃ (ዶ/ር) በአብዛኛው የተቋሙ ዕቅድ 100ና ከዚያ በላይ መፈፀሙ የሚበረታታ እና ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑን ገልፀዋል። ሴቶችን ለአመራርነት ለማብቃት የተጀመሩ ስራዎች፣ አደንዛዥ እፅና ከመጤ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለመከላከል እያከናወነ ያለውን ተግባር ይበልጥ ማጠናከር እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በበጎ ፍቃድ አገልግሎት ወጣቶችና ህፃናት የነገይቱን ኢትዮጵያ ለመገንባት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ማድረግ መቻሉን ገልፀው፤ አገልግሎቱን የበለጠ ለማስፋት በትኩረት ሊሰራ ይገባልም ብለዋል።
የመኖሪያ አካባቢን ምቹ ለማድረግና ገጽታን ለመቀየር የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 10, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦በህብረተሰብ ተሳትፎ የመኖሪያ አካባቢን ምቹ ለማድረግና ገጽታን ለመቀየር የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአዲስ አበባ ከተማ የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ፀሐይ ኪባሞ ገለጹ፡፡ ኮሚሽኑ ዛሬ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 በ2018 ዓ.ም. በህብረተሰብ ተሳትፎ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን በይፋ አስጀምሯል። በወረዳው የብሩህ ኮከብ የጋራ መኖሪያ ቤት ውስጥ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ከሚከናወኑ የልማት ስራዎች መካከልም የሕፃናት የመዝናኛ ስፍራ፣ የከርሰ ምድር ውሃ ፣የውስጥ ለውስጥ መንገዶችና እና ሌሎች የልማት ስራዎች ይገኙበታል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ፀሐይ ኪባሞ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በርካታ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በመንግስትና በሕዝብ ተሳትፎ አማካኝነት ከተማዋን ምቹ የመኖሪያ ስፍራ ለማድረግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት እየተከናወኑ ባሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችም ህብረተሰቡ በእውቀቱ፣ በገንዘቡና በጉልበቱ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተያዘው በጀት ዓመት መዲናዋን ምቹና ለመኖሪያ ተመራጭ ለማድረግ ህብረተሰቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የወረዳ 4 ዋና ስራ አስፈፃሚ ማርታ ተፈራ በበኩላቸው፤ መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በማጠናቀቅ እያስመዘገበ ካለው ስኬት ልምድ በመውሰድ ውጤታማ ስራዎችን ለማከናወን ይሰራል ብለዋል፡፡ በወረዳው በብሩህ ኮከብ የጋራ መኖሪያ ቤት በዛሬው እለት የተጀመሩት የተለያዩ የልማት ስራዎች ህብረተሰቡን በማሳተፍ በፍጥነት እንዲጠናቀቁ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። የጋራ መኖሪያ መንደሩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ኢንጂነር ግርማ ገብረማርያም በበኩላቸው፤ በመኖሪያ መንደሩ ውስጥ 30 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ የተለያዩ ልማት ስራዎችን ለማከናወን መታቀዱን ተናግረዋል፡፡ የጋራ መኖሪያው ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ማርያም ዮሴፍ፤ አካባቢውን በማልማት ለኑሮ ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠቃሚ እንደሚያደርጋቸው ጠቁመዋል፡፡
በተቀናጀ መንገድ ሕገ-ወጥ የውጭ ምንዛሪ አሻጥሮችን ሲፈጽሙ የተደረሰባቸው አንድ መቶ አስራ ሁለት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር ዋሉ
Nov 10, 2025 209
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦በተቀናጀ መንገድ ሕገ-ወጥ የውጭ ምንዛሪ አሻጥሮችን ሲፈጽሙ የተደረሰባቸው አንድ መቶ አስራ ሁለት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳስታወቀው፥ መንግሥት ተግባራዊ ያደረገውን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በመጻረር በተደራጀ መንገድ በሚፈጽሙ ሕገ-ወጥ የውጭ ምንዛሪ አሻጥሮች ዙሪያ በተቀናጀ መልኩ ምስጢራዊ የመረጃ ስምሪት ሲከናወን ቆይቷል፡፡ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት፣ የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት፣ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ፣ የክልል የፀጥታ አካላት እና በህብረተሰቡ ጥቆማ በተደረገ የተቀናጀ ሥምሪት በፋይናንስ አሻጥር የተሰማሩ አንድ መቶ አስራ ሁለት ኢትዮጵያውያንና የተለያዩ የውጭ ሀገር ዜግነት ያላቸው ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን፤ ከሕገ -ወጥ ተግባሩ ጋር ትስስር የነበራቸው አምስት መቶ አስራ ዘጠኝ የባንክ አካውንቶች መታገዳቸውን እንዲሁም የተለያዩ ኤግዚቢቶች መያዛቸውን መግለጫው አመልክቷል፡፡ ሕገ- ወጥ ሃዋላዎች ፣ የገንዘብ ዝውውሮች፣ የውጭ ምንዛሪ ስወራዎች ፣ የግብር ስወራዎች፣ ሕገ- ወጥ ገንዘብን ሕጋዊ የማስመሰልና ሌሎች ተመሳሳይ ወንጀሎች በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሲያስከትሉ እንዲሁም አሸባሪዎችንና የታጠቁ ቡድኖችን ለመደገፍ ሲውሉ መቆየታቸውን መግለጫው አመልክቷል፡፡ በተለይም ሕገ- ወጥ በሆኑ ዓለም አቀፍ የገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች፤ ሕገ- ወጥ የውጭ ምንዛሪ ማስተላለፊያ መተግበሪያዎች፤ የክሪፕቶ ከረንሲ መተግበሪያዎች፤ ሕገ-ወጥ የሃዋላ አዘዋዋሪዎችና ደላላዎች፤ በወጪና ገቢ ንግድ ላይ አሻጥር የፈፀሙ አስመጪዎችና ላኪዎች እንዲሁም ሕጋዊ ንግድ ሳይኖራቸው በሕገ-ወጥ ሃዋላ ላይ በመሰማራት ከፍተኛ ገንዘብ በማንቀሳቀስ በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ባደረሱ አካላት የማያዳግም ሕጋዊ እርምጃ መወሰዱን መግለጫው ጠቁሟል፡፡ በተለያዩ ዓለማት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የሚልኩት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገባ የብሔራዊ ባንክን መመሪያ በሚጥስ ሁኔታ በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሲያስከትሉ የቆዩ ሕጋዊ ፈቃዳቸው በፈጸሙት ተደጋጋሚ ጥፋት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተሰረዘባቸው ዓለም አቀፍ የሃዋላ አስተላላፊዎችና ሕገ-ወጥ የሃዋላ ድርጅቶችም እርምጃው የተወሰደባቸው ናቸው ብሏል። በተጨማሪም በሀገር ውስጥ ሕገ- ወጥ የውጭ ምንዛሪ ማስተላለፊያ መተግበሪያዎችን በመጠቀም ሀብትን ከሀገር በማሸሽ ላይ ያሉ ድርጅቶች ባለቤቶችም በቁጥጥር ሥር ውለዋል ነው ያለው። የብሔራዊ ባንክ ሕግን በሚጥስ ሁኔታና ያለምንም ፈቃድ የክሪፕቶ ከረንሲ መተግበሪያን በመጠቀም በሕገ- ወጥ መንገድ የውጭ ምንዛሪን ሲያዘዋውሩ የነበሩ አካለት ላይም እርምጃ መወሰዱንም መግለጫው አመልክቷል፡፡ በሀገሪቱ ብሔራዊ ጥቅም ላይ በማነጣጠር ሲፈጸም የነበረው ኢኮኖሚያዊ አሻጥር ትላልቅ የመንግሥት ፕሮጀክቶችን ለማስተጓጎል፤ ሕዝብ በመንግሥት ላይ ቅሬታ እንዲያድርበት እንዲሁም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እንዳያንሰራራ በተቀናጀ መንገድ ሲፈጽሙት የነበረ መሆኑንም አንስቷል፡፡ የሀገርን ደኅንነት ስጋት ላይ በሚጥሉ እና የሀገርን ኢኮኖሚ በሚጎዱ አሻጥሮች ላይ ተሳታፊ የሆኑ አካላትን በመከታተል የማያዳግም እርምጃ ለመውሰድ የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በመግለጫው፥ መላው ሀገር ወዳድ ዜጋ መሰል ወንጀሎችንና ወንጀለኞችን በማጋለጥ እያደረገ ያለውን ተሳትፎ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርቧል፡፡
በተለያዩ አገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል-የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Nov 10, 2025 144
አዲስ አበባ፤ህዳር 1/2018 (ኢዜአ)፦በተለያዩ አገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ወደ አገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አመልክቷል። ዜጎች ከህገ ወጥ ጉዞ ራሳቸውን እንዲጠብቁም አሳስቧል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ በተለያዩ አገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን አመልክቷል። ከውጭ ግንኙነት ቁልፍ ሥራዎች አንዱ የዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ መሆኑን የገለጸው ሚኒስቴሩ፥ በፖሊሲው አማካኝነት በውጭ አገር የሚኖሩ ዜጎቻችን መብት የማስከበር፣ ለዜጎች ተገቢ የቆንስላ አገልግሎት የመስጠት፣በሄዱበት ሀገር ህጋዊ የመኖሪያ ፍቃድ የሌላቸውና የሀገሩ መንግሥት ዜጎቻችን ሀገራቸውን እንዲለቁ ሲወስን መብታቸው፣ ክብራቸውና ደህንታቸው ተጠብቆ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል። በዚህም መሠረት ባለፉት አራት ዓመታት በተለያዩ የመካከለኛ ምስራቅ፣የአፍሪካ እና እንደ ማይናማር ያሉ የእስያ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ከ500 ሺህ በላይ ዜጎቻችንን ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ ማድረግ መቻሉን ጠቁሟል። ከመስከረም 5 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በሳዑዲ አረቢያ በተለያዩ እስር ቤቶችና ማቆያ ማዕከላት የሚገኙ ከ17 ሺህ በላይ ዜጎቻችን መመለስ መቻሉንና በአሁኑ ወቅትም በሳዑዲ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች የመመለሱ ሥራ መቀጠሉን በመግለጫቸው ላይ ተመላክቷል። በተመሳሳይ በየመን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ 36 ዜጎች ወደሀገራቸው እንዲመለሱ የተደረገ ሲሆን ሌሎችንም አስፈላጊውን የሰነድ ማጣራት በማድረግ የጉዞ ሰነድ በማዘጋጀት ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት እንዲሁም ከዓለም ዓቀፉ የፍልሰተኞች ድርጅት (አይኦኤም) ጋር በመቀናጀት እየሰራ መሆኑን ገልጿል። በማይናማር፣ላኦስ እና ካምቦዲያ እንዲሁም በሌሎች ሀገራት በተመሳሳይ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎቻችን የመመለስ ጥረት መቀጠሉንም እንዲሁ። ሆኖም ግን አሁንም ድረስ ዜጎች በተሳሳተ መረጃ በሕገ-ወጥ ደላሎች ተታለው ወደ ተለያዩ ሀገራት በመጓዝ ለእስራት እና ለሞት እየተዳረጉ መሆኑንና መንግሥት ዜጎች ከህገወጥ ጉዞ ራሳቸውን እንዲከላከሉ እና እንዲጠነቀቁ ነው ሚኒስቴሩ ያሳሰበው። ወደ ውጭ ሃገራት የሚደረጉ ጉዞዎችና የስራ ቅጥሮች በህጋዊና መንግስት ባስቀመጠው አሰራር ብቻ ሊሆን እንደሚገባም አስገንዝቧል።
በሰው ተመርተን መጥተን በራሳችን ተመልሰናል-ታካሚዎች
Nov 10, 2025 82
ደሴ ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ በደሴ ከተማ ቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል በተደረገላቸው ነፃ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ሕክምና በሰው ተመርተው መጥተው የዓይን ብርሃናቸው ተመልሶ በራሳቸው መመለስ በመቻላቸው መደሰታቸውን ታካሚዎች ገለጹ። ሆስፒታሉ ለአንድ ሳምንት በዘመቻ በሰጠው ነጻ የዓይን ቀዶ ሕክምና አንድ ሺህ 730 ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስታውቋል። ታካሚዎቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት ፤ በሆስፒታሉ በተደረገላቸው ነፃ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ሕክምና በሰው ተመርተው መጥተው የዓይን ብርሃናቸው ተመልሶ በራሳቸው መመለስ በመቻላቸው ተደስተዋል። በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ዝቋላ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ ዘነቡ ፈንታዬ፤ ሁለቱም ዓይናቸው ማየት ካቆሙ ሦስት ዓመታት እንዳለፉ አስታውሰዋል። በዚህም ማህበራዊ እንቅስቃሴያቸው ተገድቦ ሲቸገሩ መቆየታቸውን ጠቅሰው፤ አሁን ባገኙት ነጻ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ሕክምና የሁለቱም ዓይኖቻቸው ሙሉ ብርሃን መመለሱን አረጋግጠዋል። ከሁለት ዓመታት በላይ የዓይን ብርሃናቸውን በማጣታቸው በጨለማ ውስጥ ለመኖር ተገደው መቆየታቸውን የገለፁት ደግሞ የሰሜን ሽዋ ዞን ደብረ ሲና ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ፈንታዬ ጌታሁን ናቸው። በሆስፒታሉ በተደረገልኝ ነጻ ሕክምና የሁለቱም ዓይኖቼ ብርሃን መመለሱ በልጆቼ እየተመራሁ መጥቼ በራሴ እያየሁ እንድመለስ ማስቻሉ ደስታን ፈጥሮብኛል ብለዋል። ለተደረገላቸው ህክምና አመስግነው አገልግሎቱ በቀጣይም ሌሎች የችግሩ ተጋላጭ ለሆኑ ወገኖች በማድረስ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም ተናግረዋል። ከደቡብ ወሎ ዞን ወግዴ ወረዳ ለህክምናው የመጡት አቶ ሀብታሙ ሽፈራው በበኩላቸው በሰው እየተመራሁ መጥቼ ባገኘሁት ሕክምና የዓይን ብርሃኔ ተመልሶ ዳግም ማየት መጀመሬ የመኖር ተስፋዬን አለምልሞልኛል ብለዋል። በዚህም ዳግም የተወለዱ ያህል ደስታ እንደተሰማቸው ጠቁመው ወደ ሆስፒታሉ ሲመጡ ሕክምናውን ለመሞከር እንጂ ብርሃናቸው ይመለሳል የሚል እምነት እንዳልነበራቸው አስረድተዋል። በሆስፒታሉ የዓይን ሕክምና ክፍል ኃላፊና የዘመቻው አስተባባሪ እንዳልክ ያረጋል በበኩላቸው ከጥቅምት 24/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለአንድ ሳምንት በተሰጠው የዓይን ሞራ ግርዶሽ ነጻ ሕክምና አንድ ሺህ 730 ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የዓይን ሞራ ግርዶሽ በይበልጥ ከዕድሜ ጋር ተያይዞ እንደሚከሰት ጠቁመው፤ በወቅቱ ካልታከመ ለዓይነ ስውርነት እንደሚዳርግ ገልጸዋል። ችግሩን ለማቃለል ሆስፒታሉ "ኪዩር ብላይንድነስ ፕሮጀክት" ከተሰኘ ድርጅት ጋር በመተባበር ሕክምናውን በዘመቻ በመስጠቱ በኢኮኖሚ ችግር ምክንያት ያልታከሙ ወገኖችን ለማገዝ አስችሏል ብለዋል። በደሴ ከተማ የሚገኘው የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ባለፉት ዓመታት በዘመቻ ብቻ 20 ሺህ ለሚጠጉ ሰዎች ነጻ የዓይን ሞራ ቀዶ ሕክምና አገልግሎት መስጠቱን ከሆስፒታሉ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የጤና አገልግሎትን ለማዘመን የተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተመዘገበባቸው ነው - ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴ
Nov 10, 2025 168
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ የዜጎችን ጤና አገልግሎት ለማዘመን የተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተመዘገበባቸው መሆኑን የኢፌድሪ ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴ ገለጹ። የጤና ሚኒስቴር የመድሀኒት አቅርቦት እና የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማሳለጥ "ጤንነቴ" የተሰኘ የሞባይል መተግበሪያ አስመርቋል። በተጨማሪም "ለበጎ" የተሰኘ የአምቡላንስ ስምሪት ስርዓትና 952 የጤና መረጃ እና ምክር አገልግሎት ነጻ የስልክ ጥሪ ማዕከልን ስራ አስጀምሯል። ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴ በዚሁ ወቅት፤ በሽታን ከመከላከል ባለፈ አክሞ ማዳን ላይ ውጤታማ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። የዜጎችን የጤና አገልግሎት ለማዘመን የተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተመዘገበባቸው መሆኑን ጠቁመው፤ በዛሬው ዕለት ይፋ የተደረጉት መተግበሪያዎችም ዜጎች ቀልጣፋ፣ ፍትሀዊና ጥራቱን የጠበቀ የጤና አገልግሎት ማግኘት የሚያስችላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በራስ አቅም የበለጸጉት እነዚህ መተግበሪያዎች የጤና ስርዓቱን በጉልህ የሚያግዙ መሆናቸውን አንስተው፤ በጤና ስርዓቱ ላይ የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ በበኩላቸው፤ የጤናውን ዘርፍ ተደራሽና ቀልጣፋ ለማድረግ ቴክኖሎጂ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። ሚኒስቴሩ የዜጎችን የጤና አገልግሎት ለማሻሻል የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ነድፎ እየሰራ መሆኑን ገልጸው በዛሬው ዕለት ወደ ስራ የገቡት መተግበሪያዎች የዚሁ አካል ናቸው ብለዋል። "ጤንነቴ" የተሰኘው መተግበሪያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ህብረተሰቡ መድሀኒቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ ታስቦ የለማ መሆኑን ተናግረዋል። "ለበጎ" የተሰኘው የአምቡላንስ ስምሪት ስርዓት እና 952 ነጻ የስልክ ጥሪ ማዕከል ለድንገተኛ የጤና አገልግሎት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም አንስተዋል። በዛሬው እለት የተመረቁት መተግበሪያዎች በአጠቃላይ የጤናውን ስርዓት የሚያሻግሩ መሆናቸውን በመጠቆም። በመርሀ ግብሩ ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴን ጨምሮ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የክልሎች ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ሀላፊ ቢልለኔ ስዩም እንዲሁም ሌሎች የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ቀኑ ወንድማማችነትንና ብዝኀነትን በሚያጠናክር መልክ ይከበራል
Nov 10, 2025 136
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 1/2018(ኢዜአ)፡- የዘንድሮው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን ወንድማማችነትና ብዝኀነትን በይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ እንደሚከበር ምክር ቤቱ አስታወቀ። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን “ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለኅብረ-ብሔራዊ አንድነት” በሚል መሪ ሐሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ ሕዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አስተናጋጅነት ይከበራል። የክልሉ የብሔረሰቦች ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተሾመ ለምጃቦ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ቀኑ በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች እንደሚከበርና በክልል ደረጃ በሳጃ ከተማ ሕዳር 22 ቀን 2018 ዓ.ም የማጠቃለያ መርሐ-ግብር ይኖራል ብለዋል። በዚህም መሠረት ቀኑን ምክንያት በማድረግ ከዛሬ ጀምሮ ለ10 ተከታታይ ቀናት በሕገ-መንግሥትና የፌደራሊዝም አስተምኅሮ ሥርፀት ላይ በየደረጃው ሥልጠና እንደሚሰጥ ጠቁመዋል። በተጨማሪም የደም ልገሳ፣ ዐቅመ ደካሞችን ማገዝና ለዐቅመ ደካማ ወላጆች ልጆች የትምህርት ቁሳቁስ ማሰባሰብን ጨምሮ ሌሎች የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶችም እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ደግሞ በወልቂጤ ከተማ ባዛርና ሲምፖዚየም እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ ሕዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም በሆሳዕና ከተማ እንደሚከበር ገልጸዋል። በዓሉን ለሚታደሙ እንግዶች ምቹ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ዝግጅቶች እየተጠናቀቁ መሆኑንም አስታውቀዋል። ቀኑ ወንድማማችነትን እና ብዝኀነትን በይበልጥ የምናጎለብትበት ነው ብለዋል። የቀኑ መከበር የአካባቢውን ቱሪዝም፣ ባህል እንዲሁም ልማት ለማስተዋወቅና የልማት ሥራዎችን በይበልጥ ለማከናወን ከፍተኛ መነሳሳት መፍጠሩንም አንስተዋል።