ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በደብረ ማርቆስ ከተማ የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የፖሊስ አባላት እውቅናና የማእረግ እድገት ተሰጠ
Nov 9, 2025 296
ደብረ ማርቆስ ፤ጥቅምት 30/2018 (ኢዜአ) ፡-የደብረ ማርቆስ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የህዝብን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ተግባር የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ አባላቱ እውቅናና የማእረግ እድገት ሰጠ ። የደብረ ማርቆስ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የህዝብን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ተግባር የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ አባላቱ ዛሬ እውቅናና የማእረግ እድገት ሰጥቷል ። የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ መምሪያ ሃላፊ ኮማንደር ቢምረው አሰፋ በስነ ስርአቱ ላይ እንዳሉት በከተማ አስተዳደሩ የህዝብን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ የላቀ አፈጻጸም ላበረከቱ የመደበኛና አድማ መከላከል ፖሊስ አባላት እውቅናና የማእረግ እድገት ተሰጥቷል ። የፖሊስ አባላቱ በተለይም ባለፉት አመታት በተከናወነ የተቀናጀ የሰላምና የጸጥታ እንዲሁም የህግ ማስከበር ተግባር የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ መሆናቸውን ተናግረዋል ። ፖሊስ የህዝቡን ሰላምና ደህንነት የማረጋገጥ ተግባሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ተወካይ አቶ መኮንን ሙሉአዳም በበኩላቸው ፖሊስ በህዝብና በመንግስት የተጣለበትን ሃላፊነት ለመወጣት ባደረገው ጥረት አበረታች ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል ። የከተማው ፖሊስ በተለይ ባለፉት ሁለት አመታት ከሌሎች የጸጥታ አካላት ጋር በመሆን ባከናወነው የጸጥታና የህግ ማከበር ተግባር በከተማውና አካባቢው አሁን ለሰፈነው ሰላም ከፍተኛ አስተዋጾ ማበርከቱን ጠቁመዋል። የተገኘው ሰላም በዘላቂነት እንዲቀጥል የትብብር ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል ። በከተማው ዛሬ እውቅናና የማእረግ እድገት ከተሰጣቸው የፖሊስ አባላት መካከል የከተማ አስተዳደሩ ሁለተኛ ፖሊስ ጣቢያ አዛዥ ኢንስፔክተር ብሩክ ሁነኛው በበኩላቸው የተጣለባቸውን ተልእኮ ለመወጣት ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ መቆየታቸውን ገልጸዋል። የተሰጣቸው እውቅናና የማእረግ እድገት ለቀጣይ ተልእኮ የበለጠ እንደሚያነሳሳቸው አመላክተዋል ። በሀገር መከላከያ ሰራዊት የ602ኛ ኮር አዛዥ ብርጋዴል ጀኔራል ሶፍያ መሀመድ በስነ ስርአቱ ላይ በክብር እንግድነት ተገኝተው ባስተላለፉት መልእክት በአካባቢው የሚከናወነው የህግ ማስከበር ስራ የሀገርንና የህዝብን ሰላምና አንድነት ለማስጠበቅ ያለመ ነው። ከፖሊስና ሌሎች የጸጥታ ሀይሎች ጋር በመቀናጀት የአካባቢውን ሰላም አጠናክሮ የማስቀጠል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል ።
የአመራሩ ቁርጠኝነት፣ በፈጠራ፣ በፍጥነትና በጥራት መስራት ለሁለንተናዊ ብልፅግና መረጋገጥ አስፈላጊ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Nov 9, 2025 329
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦ የአመራሩ ቁርጠኝነት፣ በፈጠራ፣ በፍጥነትና በጥራት መስራት ለሁለንተናዊ ብልፅግና መረጋገጥ አስፈላጊ ነው ሲሉ የብልፅግና ፓርቲ ፕሬዝዳንትና የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለፁ። "በመደመር መንግሥት እይታ፣ የዘርፎች እምርታ" በሚል መሪ ሀሳብ ከፌደራል፣ ከክልል፣ ከዞን እንዲሁም ከከተማ አስተዳደሮች ለተውጣጡ ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ለተከታታይ 11 ቀናት ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል። የብልፅግና ፓርቲ ፕሬዝዳንትና የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በመደመር መንግሥት ላይ የማጠቃለያ ስልጠና ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማጠቃለያ ስልጠና ላይ እንደገለፁት የአመራሩ ቁርጠኝነት፣ በፈጠራ፣ በፍጥነትና በጥራት መስራት ለሁለንተናዊ ብልፅግና መረጋገጥ አስፈላጊ ነው። በስልጠናው የመደመር መንግሥት ፅንሰ ሀሳብ፣ መንገድና መዳረሻ ግቦቹ የተዳሰሱ ሲሆን በዚህም በመደመር መንግሥት መርህ የሚመራው ፓርቲው አመራሮች በፈጠራ፣ በፍጥነትና በብዛት ስራዎችን በማከናወን የህዝባችን ሁለንተናዊ ጥያቄ ከመመለስ በላይ የሀገራችን ራዕይ ለማሳካትና ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥ በሚረዳ መንገድ መምራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትኩረት የሚሹ ግቦችን በየፈርጁ በመለየት አቅጣጫ ያስቀመጡ ሲሆን ፋይዳ፣ 5 ሚሊዮን ኮደሮች፣ የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ስራዎች፣ የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች፣ የምርጫ ምቹነትና የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም አጀንዳዎች በ100 ፐርሰንት ለማሳካት መትጋት የሚገባን ግቦች ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማጠቃለያ ገለጻ እንዳብራሩት መደመር ትውልድን ወደ ብልፅግና የሚያደርስ መንገድ ነው። የመደመር መንግሥት ለሀገር ብልፅግና ባለአደራ መሆኑን ተናግረው በፈጠራና በፍጥነት ጥራትና ብዛትን እውን ማድረግ ይገባል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለው እንዳብራሩት በብዝሀ ዘርፍ ትስስር ወደ ስልጣኔ ሽግግር ማምጣት ይገባል። የሀሳብ ሉዐላዊነት የብልፅግና መሰረት እንደሆነ የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሁሉም የፓርቲው አመራር በዚህ አግባብ በመትጋት ሁለንተናዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ አለበት ብለዋል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ባለፉት 11 ቀናት በስልጠና በውይይትና በመስክ ጉብኝትና በማጠቃለያው ገለጻ ያገኟቸውን እውቀትና ልምዶች በዕቅድ በማካተትና ወደ ስራ በመቀየር የሀገሪቱን ሁለንተናዊ ብልፅግና እውን ለማድረግ በሚደረግ ጥረት ውስጥ የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
ለብልጽግና ፓርቲ አመራሮች ሲሰጥ የቆየው ስልጠና የፓርቲው ፕሬዚዳንት እና የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት የስራ መመሪያ ተጠናቀቀ
Nov 9, 2025 308
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦ ለብልጽግና ፓርቲ አመራሮች ሲሰጥ የቆየው ስልጠና የፓርቲው ፕሬዚዳንት እና የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት የስራ መመሪያ ተጠናቋል። የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት እና የዋናው ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አደም ፋራህ እንዳስታወቁት "በመደመር መንግሥት ዕይታ፣ የዘርፎች እመርታ" በሚል መሪ ሀሳብ ለብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ከጥቅምት 19 እስከ 30 በአዳማ ከተማ እና በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ሲሰጥ የቆየው ስልጠና የብልጽግና ፓርቲ ፕሬዚዳንት ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት የስራ መመሪያ ዛሬ በስኬት ፍፃሜውን አግኝቷል ብለዋል። ከመላው ኢትዮጵያ የተውጣጡ ወደ 2000 የሚጠጉ የፓርቲያችን አመራሮች የተሳተፉበትና የአስተሳሰብ አንድነት ከመፍጠርና የተግባር አፈፃፀምን ከማላቅ አኳያ እጅግ ከፍተኛ ፋይዳ በተገኘበት በዚህ ስልጠና ፓርቲያችን እውነተኛ የህብረ ብሔራዊነት ተምሳሌት መሆኑም በተጨባጭ የተንፀባረቀበት ነበር ሲሉም ገልጸዋል። ይህ የስልጠና መርሀ ግብር ከዝግጅት እስከ ገለፃ፣ የቡድን ውይይት፣ ተሞክሮ ልውውጥ፣ የልማት ሥራዎች የመስክ ጉብኝት እና ማጠቃለያ ድረስ ዓላማውን በሚገባ አሳክቶ እንዲጠናቀቅ ኃላፊነታችሁን ለተወጣችሁ አስተባባሪዎች፣ አሰልጣኞች፣ አወያዮች፣ የፀጥታ ተቋማት፣ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት እና ልዩ ልዩ ተቋማቱ፣ የአዳማ ከተማ አስተዳደር፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የስልጠናው ተሳታፊ አመራሮች በሙሉ ላበረከታችሁት ከፍተኛ አስተዋፅዖ በብልፅግና ፓርቲ ስም ልባዊ ምስጋና ለማቅረብ እወዳለሁ ብለዋል አቶ አደም ፋራህ በመልዕክታቸው።
በመደመር መንግሥት ዕይታ በዘርፎች ላይ የመጣውን እመርታዊ ለውጥ በተጨባጭ ማየት ችለናል - የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች
Nov 8, 2025 286
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፦በመደመር መንግሥት ዕይታ በዘርፎች ላይ የመጣውን እመርታዊ ለውጥ በተጨባጭ ማየት መቻላቸውን የብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አባላት ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአባላቱን አቅም በሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ በአዳማ ከተማ መሰጠቱ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት በሀገሪቷ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ላይ ያጠነጠኑ ስልጠናዎችን ወስደዋል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ትናንት በአዳማ ዛሬ ደግሞ በአዲስ አበባ ባደረጉት ጉብኝት በግብርና እና ከተማ ልማት የተከናወኑ ስራዎችን ተመልክተዋል። የሶማሌ ክልል ርዕሰ-መስተዳደር ሙስጠፌ መሃመድ፤ የብልጽግና ፓርቲ ብዝሃ ዘርፍ ላይ ትኩረት በማድረግ በርካታ ድሎችን ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል። በግብርና ኢንዱስትሪ፣ በከተሞች ልማትና በቱሪዝም ዘርፎች የተደረጉ ሪፎርሞችና የተገኙ ውጤቶች የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር መሰረት መጣላቸውንም አንስተዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መሰተዳደር ጥላሁን ከበደ በበኩላቸው፤ ስልጠናው ኢትዮጵያ ያላት ጸጋዎች ከራሷ አልፎ ለሌሎች የሚተርፍ መሆኑን ያየንበት ነው ብለዋል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት በነበራቸው ቆይታ በተለያዩ ዘርፎች ላይ እየተከናወኑ ስላሉ ስራዎችና ስለተገኙ ውጤቶች የልምድ ልውውጥ ማድረጋቸውንም ነው የተናገሩት። የሶማሌ ክልል ርዕሰ-መስተዳደር ሙስጠፌ እንዳሉት፤ በመደመር እይታ በፈጠራና በፍጥነት ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑን ተመልክተናል ብለዋል። ኢትዮጵያ ከቀጣናው አልፋ ከዓለም አገራት ጋር ተወዳዳሪ የመሆን አቅም እንዳላትና ለዚህ ደግሞ አመራሩ በቁርጠኝነት እንዲሰራ መነሳሳትን የፈጠረ መሆኑንም ገልጸዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መሰተዳደር ጥላሁን እንደተናገሩት፤ በመደመር መንግሥት ዕይታ በዘርፎች ላይ የመጣውን እመርታዊ ለውጥ በተጨባጭ ማየት ተችሏል።
ምሩቃን የፖሊስ አባላትና መኮንኖች ለህገ መንግሥቱ ታማኝ በመሆን ሙያዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል- ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Nov 8, 2025 289
ቡልቡላ ፤ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ):- ምሩቃን የፖሊስ አባላትና መኮንኖች ለህገ መንግሥቱ ታማኝ በመሆን ሙያዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል ሲሉ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) አስገነዘቡ፡፡ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በኦሮሚያ ፖሊስ ኮሌጅ በቡልቡላ መሰረታዊ ወታደራዊ የፖሊስ ማሰልጠኛ ማዕከል ያሰለጠናቸውን የመጀመሪያ ዙር ምልምል የፖሊስ ሰልጣኞችንና 2ኛ ዙር እጩ መኮንኖችን ዛሬ አስመርቋል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የልማት እቅዶችን ተግባራዊ ለማድረግና ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን የዜጎች የነቃ ተሳትፎ ይጠይቃል፡፡ በተለይም የፖሊስ አባላት በታማኝነትና በቅንነት ህዝባቸውን በማገልገል ሙያዊ ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡ የፖሊስ አባላት ማህበረሰቡን በስነ ምግባር በማገልገል የክልሉን ሰላምና ልማት ማጠናከር ላይ ያላቸውን ድርሻ እንዲያጠናክሩም አሳስበዋል፡፡ የዛሬ ምሩቃን የፖሊስ አባላትና መኮንኖችም ለሰንደቅ ዓላማና ለህገ መንግሥት ታማኝ በመሆን ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡም አስገንዝበዋል፡፡ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሽመልስ ካሳ በበኩላቸው ኮሚሽኑ የክልሉን ፖሊስ በሰው ኃይል በማደራጀት ለክልሉ ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ምሩቃንም የማህበረሰብ አቀፍ ወንጀል መከላከል የፖሊስ አገልግሎትን በመተግበር ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚጠበቅባቸውም ተናግረዋል፡፡ በስልጠና ቆይታቸው ያገኙትን ለተልዕኮ ዝግጁ የሚያደርጉ ክህሎት በመጠቀም በታማኝነት ማህበረሰቡን ማገልገል እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል ድሪባ መኮንን እንደገለፁት የተጀመሩ የልማት እቅዶችን እውን ለማድረግ ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ለዚህም የሁለቱን አጎራባች ክልሎችን ዘላቂ ሰላም በማስጠበቅ የማህበረሰቡን የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ቅንጅታዊ ጉዞን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። "ኮሌጁ በሀገር አቀፍ ደረጃ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈንና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሌጅ ዋና ዳይሬክተር ረዳት ኮሚሽነር ጎሳዬ ከበደ ናቸው፡፡ ኮሌጁ ክልላዊ ትስስርን በማጠናከር ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጋር በመተባበር የፖሊስ አካላትን ሲያሰለጥን መቆየቱን አስታውሰው ዘላቂ ሰላም ለማስፈን የሚያግዙ ስልጠናዎች በብቃት እንደተሰጠም ተናግረዋል፡፡
ብልጽግና የዜጎችን ተጠቃሚነት በማሳደግ በሃሳብ ጥራት ላይ የተመሰረተ ተጨባጭ ስኬት እያስመዘገበ ነው
Nov 8, 2025 173
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018(ኢዜአ)፦የብልጽግና ፓርቲ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማሳደግ በሃሳብ ጥራት ላይ የተመሰረተ ተጨባጭ ስኬት እያስመዘገበ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአባላቱን አቅም በሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ስልጠና በሀገሪቷ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፤ ስልጠናው በርካታ አዳዲስ የልማት ዕውቀትና እሳቤዎች የተሰጡበት ነው ብለዋል። በስልጠናውም ላይ የኢትዮጵያን ቀጣይ አቅጣጫና አሁናዊ የልማት አቋም ታሳቢ በማድረግ አቅምና ክህሎትን የሚገነቡ በርካታ ርዕሰ ጉዳዮች መቅረባቸውን ገልጸዋል። የብልፅግና ፓርቲ የሃሳብ ጥራት ያለው፣ የገባውን ቃል በተግባር የሚፈጽም የሁለንተናዊ ዕድገት መሰረት እየሆነ መምጣቱንም ገልጸዋል። ፓርቲው ሕብረ ብሔራዊነትን የሚያስጠብቅና ሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሚሳተፉበት የሀገራዊ አንድነት መገለጫ እንደሆነም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያን የልማት ጉዞ ወደላቀ ከፍታ ለማሸጋገር በተከናወኑ ተግባራት በቱሪዝም፣ በገጠርና ከተማ፣ በኢንዱስትሪ የልማት መስኮች እመርታዊ ስኬት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የዕድገት አለኝታ ተብለው በተለዩ የኢኮኖሚ መስኮች የሀገርን ሁለንተናዊ ብልፅግና ማሳካት የሚያስችል ተጨባጭ ስኬት መመዝገቡን አስረድተዋል። ስልጠናው የኢትዮጵያን ጸጋዎች ጥቅም ላይ ለማዋል ከፍተኛ ቁጭትና ተነሳሽነትን የፈጠረ ወሳኝ የአቅም ግንባታ መድረክ መሆኑን አንስተዋል። የአፋር ክልል የማዕድን ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ መሐመድ ሁመድ፤ በስልጠናው የመደመር መንግሥትን የዘርፎች የመልማት ዕምቅ አቅም መገንዘባቸውን ገልጸዋል። ስልጠናው የዘርፎችን የተሰናሰለና ተመጋጋቢ የልማት አቅም ወደ ተግባር ለመቀየር የሚያስችል ዕውቀትና ክህሎት ያገኙበት መሆኑንም ጠቁመዋል። የጋምቤላ ክልል ሚሊሻ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ኳንግ ዑኳይ፤ የብልፅግና ፓርቲ ስልጠና ለቀጣይ ስራቸው ዕውቀትና ክህሎትን የቀሰሙበትና ዘመኑን የዋጀ መሆኑን ገልጸዋል። በቆይታቸውም የተሻለ አፈፃጸም ካስመዘገቡ የፌደራል ተቋማትና ክልሎች ልምድና ተሞክሮ መቅሰማቸውን አንስተዋል።
የኢትዮጵያና ጃፓን የዲፕሎማሲ ግንኙነት በዘርፈ ብዙ የትብብር መስኮች ተጠናክሮ ቀጥሏል
Nov 8, 2025 244
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያና ጃፓን የዲፕሎማሲ ግንኙነት በዘርፈ ብዙ የትብብር መስኮች ተጠናክሮ መቀጠሉን በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሺባታ ሂሮኖሪ ገለጹ። የጃፓን የባህል ቀን በዛሬው ዕለት የተለያዩ ሀገራት የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ እና የተለያዩ ታዳሚዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ተከብሯል። በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሺባታ ሂሮኖሪ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በሁለቱ አገራት መካከል በጋራ መግባባት ላይ የተመሰረተ ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አለ። የጃፓን መንግሥት ለበርካታ ኢትዮጵያውያን የትምህርት ዕድል መስጠቱን አመልክተው፤ በየጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) የሥልጠና ፕሮግራሞች አማካኝነት በርካታ ሰልጣኞች ዕድሉን ማግኘታቸውን ጠቁመዋል። የሀገራቱን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን በማሳደግ ረገድ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም አንስተዋል። ጃፓንና ኢትዮጵያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸው ከመሰረቱበት ጊዜ አንስቶ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። ይህም በአፍሪካ ከጃፓን የመጀመሪያዎቹ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች አንዱን እንደሚወክል ገልጸው፤ ግንኙነቱም በፖለቲካዊ፣ በኢኮኖሚ፣ በባህላዊና ሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። ጃፓን እንደ ትምህርት፣ ጤናና ግብርና ባሉ መስኮች የገንዘብና የቴክኒክ ትብብርን ማስፋፋቷን አንስተዋል። የጃፓንና ኢትዮጵያን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከርም ጥረታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉም ገልጸዋል። በባህልና እና ስፖርት ሚኒስቴር የስራ አመራር ዋና ስራ አስፈጻሚ አህመድ መሀመድ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያና ጃፓን ጠንካራ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን ገልጸዋል። በዓሉ በኢትዮጵያና በጃፓን መካከል እያበበ ላለው ሕያው የባህል ግንኙነት ሁነኛ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰዋል። እንዲሁም መሰል በዓላት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን በማጠናከር ረገድ ጉልህ ፋይዳ እንዳላቸው አመልክተዋል።
ጽንፈኛውን ቡድን ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም እንታገላለን
Nov 8, 2025 192
ወልዲያ፤ ጥቅምት 29/2018(ኢዜአ)፡- በተለያዩ አጋጣሚዎች እገታና ዘረፋ እየፈፀመ ያለውን ጽንፈኛ ቡድን ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም እንታገላለን ሲሉ የአሽከርካሪዎች ማህበራት ተናገሩ። "የባዳና የባንዳን ሴራ በማምከን አንፀባረቂ ድሎችን እናስመዘግባለን "በሚል መሪ ሀሳብ በወልዲያ ከተማ ከባጃጅ፣ ከታክሲና ሌሎች የተሽከርካሪ ማህበራት ጋር በሰላምና ጸጥታ ጉዳይ ላይ ውይይት ተካሂዷል። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል ወጣት ፋሲካው መስፍን ፣አቶ ምህረቴ መኮንን እና ወጣት ጋሻው አለማየሁ በሰጡት አስተያየት፤ አሁን ላይ ሕዝቡ በሰላም መስራት፣ ወጥቶ መግባትና የልማት ስራዎችን ለማሳካት በከፍተኛ ፍላጎትና ተነሳሽነት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሕዝቡ ፍላጎትና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ይህ ቢሆንም እየተሹለከለከ አገታ፣ ዘረፋና ግድያ እየፈፀመ ያለው ጽንፈኛ ቡድን ችግር እየፈጠረ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በተለያዩ አጋጣሚዎች እገታና ዘረፋ እየፈፀመ ያለውን ጽንፈኛ ቡድን ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም እንታገላለን ሲሉ አረጋግጠዋል። የውይይት መድረኩን የመሩት በመከላከያ ሰራዊት የ11ኛ ዕዝ ምክትል አዛዥ ለኦፕሬሽናል ሜጀር ጄኔራል ዘውዱ ሰጥአርጌ፤ ጽንፈኛው ከታሪካዊ ጠላቶች ጋር በመተባበር የህዝብን ሰላም ለማናጋትና የሀገርን ጥቅም ለማሳጣት እየሰራ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የህዝብ ጠላትና የልማት ጸር የሆነውን ጽንፈኛ ቡድን በመከታተል ጠንካራ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ገልጸው እርምጃው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በዚህ ጥረት ውስጥ የህዝቡን ትብብርና እገዛ አድንቀው፤ በወንጀል እንቅስቃሴ ውስጥ ያሉ አካላትን በማጋለጥና መረጃ በመስጠት ጭምር የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች የላቀ ሚናቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።
የምሥራቅ ዕዝ በየተሰማራበት የግዳጅ ቀጣና ተልዕኮውን በላቀ ብቃትና ቁርጠኝነት መወጣቱን አጠናክሮ ቀጥሏል-ሜጀር ጄነራል ፍቃዱ ፀጋዬ
Nov 8, 2025 175
ጅግጅጋ፤ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፡-የምሥራቅ ዕዝ በየተሰማራበት የግዳጅ ቀጣና ተልዕኮውን በላቀ ብቃትና ቁርጠኝነት መወጣቱን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠሉን የዕዙ ምክትል አዛዥ ሜጀር ጄነራል ፍቃዱ ፀጋዬ ገለጹ። ዕዙ በማሰልጠኛ ማዕከሉ የአቅም ግንባታ ማጠናከርያ ስልጠና የሰጣቸውን ወታደሮች አስመርቋል። በምረቃው ሥነ- ሥርዓት ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የምሥራቅ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጀር ጀnራል ፍቃዱ ፀጋዬ እንደገለጹት፤ ዕዙ የሀገርን ሉዓላዊነትና የሕዝቦችን ደሕንነት በላቀ ብቃትና ጀግንነት እያስጠበቀ ይገኛል። በተለይ ዕዙ በተለያዩ ጊዜ የተሰጠውን ተልዕኮና ግዳጅ በላቀ ብቃት ስኬታማ አፈፃፀም እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል። የሕዝቦችን ሰላምና ደሕንነት የሚነሱ ጽንፈኞችንና ተላላኪዎችን በመደምሰስ አኩሪ ገድል መፈፀሙንም አንስተዋል። የምሥራቅ ዕዝ በየተሰማራበት የግዳጅ ቀጣና እና አካባቢ ተልዕኮውን በላቀ ብቃት፣ ቁርጠኝነትና ጀግንነት መወጣቱን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠሉን ሜጀር ጄነራል ፍቃዱ ፀጋዬ አረጋግጠዋል። ስልጠናውም የሠራዊቱ አባላት በማንኛውም ጊዜና በየትኛውም ቦታ ለሚፈጠር የፀጥታ ስጋት ተገቢውን ምላሽ መስጠት የሚያስችልና የተሟላ የዝግጁነት ቁመና የገነባ ነው ሲሉ ገልጸዋል። የሠራዊቱ አባላትም በማዕከሉ ያገኙትን ክሕሎት በመጠቀም ሕገ መንግስታዊና ተቋማዊ ተልዕኮን በጀግንነት ታጥቀውና ሕዝባዊ ባሕሪ ተላብሰው መወጣት እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። የምሥራቅ ዕዝ ማሰልጠኛ ማዕከል አዛዥ ኮለኔል አሊ ሰዒድ በበኩላቸው፤ ተመራቁ የሰራዊቱ አባላት ከዕዙ የተለያዩ ኮሮች የተውጣጡ መሆናቸወን ተናግረዋል። የሠራዊቱ አባላት በማዕከሉ ቆይታቸው ዘመናዊ ወታደራዊ ዕውቀትና ጥበብ የቀሰሙ መሆናቸውን ጠቁመው፥ በስልጠና ቆይታቸው ያገኙት እውቀትም የሚሰጣቸውን ግዳጅ በብቃት እንዲወጡ የሚያግዝ ነው ብለዋል። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የዕዙ ከፍተኛ መኮንኖች፣የሶማሌና ሐረሪ ክልል የፖሊስ ኮሚሽነሮችና ሌሎች አመራሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና የሚያስቀጥል እመርታዊ የዕይታ አቅም ፈጥሯል
Nov 8, 2025 186
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና የሚያስቀጥል እመርታዊ የዕይታ አቅም መፍጠሩን የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር ስልጠና ተሳታፊዎች ገለጹ። ፓርቲው ሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሚሳተፉበትን አካታችና አቃፊ ምኅዳር በመፍጠር ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እየሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የብልጽግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአባላቱን አቅም የሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰሞኑን በአዳማ ከተማ ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ሥልጠና በሀገሪቷ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮረ እንደነበር ተገልጿል፡፡ ከፍተኛ አመራር አባላቱም ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የግብርና ስራዎችን ጎብኝተዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ፤ ስልጠናው የኢትዮጵያን የማንሰራራት ዘመን በማጽናት የግብርና ኢንዱስትሪ ሽግግርን የሚያፋጥን ዕውቀትና ክህሎት የተገኘበት ነው ብለዋል። የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ፣ ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ዕድገትን በማሳለጥ የኢንዱስትሪ ሽግግርን ማፋጠን የሚያስችል የአመራር ዕውቀትና ክህሎት የተገኘበት መሆኑን ገልጸዋል። በቱሪዝም፣ በግብርና ትራንስፎርሜሽን፣ በኢንዱስትሪና ከተማ ልማትን ስራዎችም ተመጋጋቢ የኢኮኖሚ ዕድገት ማሳለጫ አቅሞች መሆናቸውንም ተናግረዋል። በብልፅግና ፓርቲ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢሳቅ አብዱልቃድር፤ የመደመር መንግሥት ዕይታ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚያስቀጥል አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ሥልጠናም የኢትዮጵያን ዕድገት ለማስቀጠል የጠራ ግንዛቤን በመያዝ ወደ ተግባር የሚገባበት ዕውቀትና ክህሎት የተገኘበት መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በቱሪዝም፣ በገጠርና ግብርና ሽግግር፣ ኢንዱስትሪ፣ ከተማ ዕድገትና የልማት መስክ አንኳር ጉዳዮች ላይ ተቀራራቢ ዕውቀትና ግንዛቤ የተገኘበት መሆኑን አንስተዋል። የብልፅግና ፓርቲ ሁሉንም ኢትዮጵያዊያን የሚሳተፉበትን አካታችና አቃፊ ምኅዳር በመፍጠር የኢትዮጵያና ዜጎቿን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የመስክ ምልከታቸውም የብልፅግና ፓርቲ ከቃል የተሻገረ ተጨባጭ ስኬት ያስመዘገቡ የልማት ስራዎችን እያከናወነ መሆኑና ማሳያ መሆናቸውን ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ሰናይት ሠለሞን፤ በአዳማ የስልጠና ቆይታቸው በቱሪዝም፣ በግብርና ትራንስፎርሜሽን፣ በአንዱስትሪና ከተማ ልማት ወሳኝ የኢኮኖሚ ዕድገት መስኮች ላይ የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማላቅ አቅም የፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። በስልጠናውም የሀገርን ሁለንተናዊ ዕድገት በተቀናጀና በተናበበ መልኩ ለመምራት ልምድና ተሞክሮ በመጋራት ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን አጽንቶ የሚያስቀጥል አቅም የተፈጠረበት መሆኑንም ተናግረዋል። በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አሕመድ አሊ፤ በስልጠናው ሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና አህትማማችነትን በማጠናከር የኢትዮጵያ ህብረት የታየበት መሆኑን ገልጸዋል። በስልጠናውም የበለጸገችና የዜጎቿ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የተረጋገጠባት ኢትዮጵያን ለመገንባት ከፍተኛ የአመራር ስምሪት የተሰጠበት መሆኑንም ገልጸዋል።
የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምልምል የፖሊስ ሰልጣኞችንና ዕጩ መኮንኖችን እያስመረቀ ነው
Nov 8, 2025 184
ቡልቡላ፤ ጥቅምት 29/2018(ኢዜአ)፡- የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ምልምል የፖሊስ ሰልጣኞችንና ዕጩ መኮንኖችን ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በተገኙበት እያስመረቀ ነው። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን በኦሮሚያ ፖሊስ ኮሌጅ በቡልቡላ መሰረታዊ ወታደራዊ የፖሊስ ማሰልጠኛ ማዕከል ያሰለጠናቸውን የመጀመሪያ ዙር ምልምል የፖሊስ ሰልጣኞችንና 2ኛ ዙር እጩ መኮንኖችን ነው በማስመረቅ ላይ የሚገኘው፡፡ ተመራቂዎቹ በስልጠና ቆይታቸው ልዩ ልዩ ፖሊሳዊ እውቀቶችንና ክህሎቶችን መቅሰማቸውም ተመልክቷል፡፡ እንዲሁም የማህበረሰቡን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ የሚሰጣቸውን ተልዕኮና ግዳጅ በብቃት ለመፈፀም የሚያስችሉ ስልጠናዎች መውሰዳቸውም እንዲሁ፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉና የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ከፍተኛ አመራሮችና ሌሎች እንግዶች እየተሳተፉ ነው፡፡
የወል ትርክት ግንባታ ይበልጥ እንዲጠናከር ሚናችንን እንወጣለን - የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት
Nov 8, 2025 115
ወላይታ ሶዶ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ):- የወል ትርክት ግንባታ ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የነቃ ተሳትፎ በማድረግ ሚናቸውን እንደሚወጡ በደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባላት ገለጹ። የወል ትርክት ብሔራዊ ጥቅምን የሚያስከብር ትውልድን በመፍጠርና ጠንካራ ሀገረ መንግስትን በመገንባት ረገድ የማይተካ ሚና እንዳለውም ተመልክቷል። የጋራ ምክር ቤቱ አባላት ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የተለያየ ስብጥር ባለው ማሕበረሰብ ውስጥ የጋራ የሆኑ ጉዳዮችን ማጠናከር ሰላምን በማፅናት ሁለንተናዊ ስኬትን ያስመዘገበች ብርቱ ሀገርን ለመገንባት ሚናው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። የጋራ ምክር ቤቱ አባልና ሰብሳቢ ጎበዜ አበራ፤ ኢትዮጵያውያን ከሚለያዩን ይልቅ የሚያቀራርቡን ነገሮች ይበዛሉ ብለዋል። ኢትዮጵያ በሕብረ ብሔራዊነት ላይ የተገነባች ሀገር ብትሆንም ከዚህ ቀደም ሲነዙ የነበሩ ከፋፋይ ትርክቶች አለመግባባት እንዲፈጠር ምክንያት እንደሆኑ አንስተዋል፡፡ በመሆኑም ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን በማጠናከርና ብሔራዊ መግባባትን በሚፈጥር የወል ትርክት ላይ አተኩሮ በመስራት ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። በሚከፋፍሉ ትርክቶች ላይ መጠመድ ኢትዮጵያዊነትን እንደማይመጥን ገልጸው፤ በመመካከር እና በመግባባት የሃገርን ከፍታ ማረጋገጥና በአለም አቀፍ መድረኮች ላይ ጎልቶ መታየት እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል፡፡ የጋራ ምክር ቤቱ አባል መምህር አለማየሁ መኮንን በበኩላቸው፤ ከፋፋይ ትርክቶች እርስ በእርስ እንዳንተማመንና በጥርጣሬ እንድንተያይ አድርገውን ቆይቷል ብለዋል። የትርክት መዛባት ቅራኔና አለመግባባቶችን እንደሚፈጥር ጠቁመው፤ የወል ትርክቶች ላይ በማተኮር ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር መስራት ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያን ስኬቶች ለማስቀጠል የአመለካከትና የተግባር አንድነት መፍጠር ተችሏል
Nov 7, 2025 261
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):-የብልጽግና ፓርቲ የከፍተኛ አመራር አባላት ሥልጠና እና የመስክ ምልከታ የኢትዮጵያን ስኬቶች ለማስቀጠል የአመለካከትና የተግባር አንድነት መፍጠር የተቻለበት መሆኑን የሥልጠናው ተሳታፊዎች ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራር የአባላቱን አቅም የሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰሞኑን በአዳማ ከተማ ስልጠና እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ስልጠና በኢትዮጵያ የግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪ እና ከተማ ልማት መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከፍተኛ አመራር አባላቱም ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን በግብርና መስክ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ሌሎች የልማት ስኬቶችን ጎብኝተዋል። በዚሁ ወቅት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ በብልጽግና ፓርቲ የከፍተኛ አመራር አባላት ስልጠና የኢትዮጵያን ዕድገት ማረጋገጥ የሚያስችል ግልጸኝነት ተፈጥሯል ብለዋል። ይህም በኢኮኖሚና ማህበራዊ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችንና የዜጎችን ብልጽግና በማስቀጠል የልማት ፍላጎቶችን በጥራትና በፍጥነት መምራት የሚያስችል የዕውቀትና ክህሎት አቅም የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። የብልጽግና ፓርቲ የከፍተኛ አመራር አባላት ስልጠና ተሳታፊዎች የወንድማማችነትና እህትማማችነት አቅሞችን በማጎልበት የተቀናጀ ተግባቦት የተፈጠረበት መሆኑን ተናግረዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፤ ግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪ ምርታማነትና የከተሞች ዕድገት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት መሠረቶች ናቸው ብለዋል። ስልጠናው በብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር አባላት ተሳታፊዎች መካከልም የዜጎችን ተጠቃሚነት ማሻሻል የሚያስችል የአመለካከትና የተግባር አንድነት ተግባቦት የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። በሌላ መልኩም የኢትዮጵያውያንን ሕብረ ብሔራዊ እሴቶች በማጎልበት ብሔራዊ መግባባት የሰፈነባት ኢትዮጵያን ማስቀጠል እንደሚያስችል አንስተዋል። በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የመስክ ምልከታ የተደረገባቸው የግብርና ዘርፍ ስኬቶችም የሀገር ውስጥ ፍላጎትን በማሟላት ለወጪ ንግድ ጭምር የሚተርፍ አቅም እየተፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። በአማራ ክልል በምክትል ርዕሰ መሥተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ እና የአማራ ክልል የከተማ እና መሠረተ ልማት ቢሮ ኀላፊ አሕመዲን መሐመድ(ዶ/ር)፤ በስልጠናው የዜጎችን ሁለንተናዊ ብልጽግና የሚያስቀጥል አቅምና ተግባቦት ተፈጥሯል ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል የምስራቅ ሸዋ ዞን የቀበሌ አደረጃጀትና የግብርና ምርታማነት ስኬቶችም የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ትምህርት የተወሰደባቸው መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም በአማራ ክልል የገጠርና ከተማን ትስስር በማጠናከር የገጠር ትራንስፎርሜሽን ስኬቶችን የበለጠ ለማስፋት በተሞክሮ የሚወሰዱ መሆናቸውን አብራርተዋል። የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ዑሞድ፤ ለፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት የተሰጠው ስልጠና እና የመስክ ምልከታ ቀጣይ ለሚከናወኑ የልማት ስራዎች ከፍተኛ ዕውቀትና ክህሎት የተገኘበት ነው ብለዋል። በስልጠናውም የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የልማት ስኬት በማስቀጠል ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገርን ማሻገር የሚያስችል የአመለካከትና የተግባር አንድነት እንደተፈጠረ ገልጸዋል። በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን በግብርና ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶች የመስክ ምልከታም የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አመርቂ ልምድና ተሞክሮ የወሰዱበት መሆኑን ተናግረዋል።
የዜጎችን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል እና ብልፅግናን እውን ለማድረግ ሕዝቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 7, 2025 183
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):- የዜጎችን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል እና ብልፅግናን እውን ለማድረግ ሕዝቡን በማሳተፍ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአመራር አባላቱን አቅም የሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰሞኑን በአዳማ ከተማ እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። ከፍተኛ አመራሮቹ ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የግብርና ክላስተር የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤በጉብኝቱ የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳኩ ውጤቶችን አይተናል ብለዋል። በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ ለውጥ የሚያመጡ ሥራዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ በስልጠናውም እነዚህን ውጤቶች በላቀ ደረጃ ማስቀጠል በሚቻልበት አቅጣጫዎች ላይ ተግባብተናል ነው ያሉት። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሕዝቡን በልማት ተጠቃሚ በማድረግ የኑሮ ሁኔታው እንዲሻሻል በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አራት የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውን ጠቁመው፤ ተጨማሪ የኮሪደር ልማት ግንባታዎችን በሌሎች አካባቢዎች ላይ ለመጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በሁሉም አካባቢዎች እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶች የብልፅግና ፓርቲ ፖሊሲዎችና አቅጣጫዎች ውጤት ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳደሩ፤ ብልፅግናን በላቀ ደረጃ ለማረጋገጥ ሕዝቡን በማሳተፉ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ፤በኦሮሚያ ክልል ያደረግነው ጉብኝት የኢትዮጵያ ብልፅግና አይቀሬነት የሚያሳይ ነው ሲሉ ተናግረዋል። ስልጠናውም ተሞክሮ ልውውጥ በማድረግ እና የጋራ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ዕድል የሰጠ መሆኑንም አንስተዋል። የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን እንዳሉት፤በክልሉ ያሉ ጸጋዎችን ጥቅም ላይ በማዋል ኢኮኖሚ እድገቱን ለማሳለጥ የሚደረገው ርብርብ ይጠናከራል። ለውጡን ተከትሎ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቁመው ውጤቱን ይበልጥ ለማስፋት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በበኩላቸው፤ አርሶ እና አርብቶ አደሩን የግበዓት አቅርቦት ችግር በመፍታት ምርትና ምርታመነት እንዲጨምር በትኩረት እንሰራለን ሲሉ ተናግረዋል። የሚገጥሙ ፈተናዎችን በጋራ በማለፍ የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስኬታማ ተግባራትን ለማከናወን በትጋት እንረባረባለን ብለዋል።
የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር ሰልጣኞች በኦሮሚያ ክልል በግብርና ምርታማነት የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን ጎበኙ
Nov 7, 2025 165
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):- የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራር ሰልጣኞች በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን በግብርና ምርታማነት የተከናወኑ ስራዎችን እና ሌሎች የልማት ተግባራትን ጎብኝተዋል። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአመራር አባላቱን አቅም በሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰሞኑን በአዳማ ከተማ እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። "በመደመር መንግሥት ዕይታ፥ የዘርፎች እመርታ" በሚል መሪ ሐሳብ በተሰጠው ስልጠና ላይ ከ2ሺህ በላይ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ ከፍተኛ አመራሮችም ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የግብርና ክላስተር የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል። የስልጠናው ተሳታፊ ከፍተኛ አመራሮችም በቱሪዝም፣ በግብርና በቴክኖሎጂና መሰል የልማት መስኮች ለቀጣይ ስራ ስንቅ የሚሆን ዕውቀትና ክህሎት የቀሰሙበትን ስልጠና መውሰዳቸውን ገልጸዋል። በስልጠናው ያገኙትን የንድፈ ሀሳብ ትምህርትም በቀጣይ ስራቸው ወደተግባር ለመለወጥ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ከሁሉም ከተማ አስተዳደሮችና ክልሎች የተወጣጡ ከፍተኛ አመራሮች በስልጠናው መሳተፋቸውም ሕብረብሔራዊ አንድነቷ የተጠበቀችና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን ያደረጉት የመስክ ምልከታም የኢትዮጵያን የዕድገት ጉዞ የሚያመላክት ተጨባጭ ስኬት መሆኑን አንስተዋል።
ብልፅግና በሀሳብ ብቻ ሳይሆን የሚገለጥ ውጤት ማስመዝገቡን በተግባር እያረጋገጠ ነው
Nov 7, 2025 166
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):- ብልፅግና ፓርቲ በሀሳብ ብቻ ሳይሆን የሚገለጥ ውጤት ማስመዝገቡን በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ፡፡ የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ሰሞኑን በአዳማ ከተማ እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራር አባላት ስልጠና በሀገሪቷ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮረ እንደነበር ተገልጿል፡፡ ከፍተኛ አመራር አባላቱም ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን ሉሜ ወረዳ የግብርና ስራዎችን ጎብኝተዋል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ ብልፅግና በሀሳብ ብቻ ሳይሆን መሬት ላይ በተጨባጭ የሚገለጥ ውጤት እያሳየ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ከአሁን በፊት እዚህ ግባ የሚባል የግብርና ሥራ የማይከናወንባቸው የአርሶ አደሩ አካባቢዎች ዛሬ ላይ አስገራሚ ውጤቶች እያስመዘገቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ብልፅግና ሲባል ከቤተሰብ የሥራ ዕድል በመፍጠር የሚጀምር መሆኑን ገልጸው፤ ዜጎች የምግብ ሉዓላዊነታቸውን ከማረጋገጥ ባሻገር ለከተማ ነዋሪዎች ምርት ማቅረብ አስችሏል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ አንዳንድ አካባቢዎች የታየው መልካም ጅምር በሁሉም የሀገሪቷ አካባቢዎች ልምድ ሆኖ እንዲቀጥል ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ አሁን የተጀመሩ ጥረቶች በሁሉም አካባቢ ቀጣይነት ሲኖራቸው የዜጎችን ተጠቃሚነት በተጨባጭ የሚያረጋግጡና የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮችና የሴክተሮች ክትትል ሚኒስትር ዴኤታ አክሊሉ ታደሰ በበኩላቸው፤ ስልጠናው በገጠርና ግብርና ትራንስፎርሜሽን፣ በመዋቅራዊ ሽግግር የግብርና ብዝሃ ምርቶችን ማስፋት የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል፡፡ በኩታ ገጠም እርሻ፣ ምርጥ ዘር በመጠቀም፣ ገበያ ተኮርና በአጭር ጊዜ የሚደርሱ የግብርና ምርቶችን በማምረት ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ፍራፍሬ በኩታ ገጠምና ምርጥ ዘር ተጠቅሞ በማልማት በውጭ ገበያ ተወዳዳሪ የሚሆን ጥራት ያለው ምርት በአጭር ጊዜ ማምረት ተችሏል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ አንዳንድ አካባቢዎች ያለውን ልምድ በሁሉም አካባቢዎች በማስፋት ቀጣይነት እንዲኖራቸው ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ የሐረሪ ብሔራዊ ጉባኤ ምክትል አፈ ጉባኤ አሚና አብዱልከሪም ለኢትዮጵያ ዕድገት የጎላ አበርክቶ ባላቸው የቱሪዝም፣ ግብርና፣ ኢንዱስትሪና ከተማ ልማት ላይ ያተኮረ ስልጠና እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡ ዘርፎቹ ኢትዮጵያን ወደ መዋቅራዊ ሽግግር የሚመሩ መሆናቸውን በመግለጽ፤ ኢትዮጵያ ያላትን አምራች ወጣት፣ ውሃና የመሬት ጸጋ በአግባቡ መጠቅም ያስችላል ብለዋል፡፡ በዚህም በግብርና ምርቶች ላይ ዕሴት በመጨመር፣ ተኪ ምርቶች ላይ በመስራት፣ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ማሻሻልና የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ በብልፅግና ፓርቲ የሶማሌ ክልል ሲቲ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሻርማርኬ ሙሀሙድ ሀሰን የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች የአቅም ግንባታ ስልጠናው በተመዘገቡ እመርታዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ ለመያዝ የሚያግዝ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በቀጣይም ኢትዮጵያን ወደ ብልፅግና ማማ ለማውጣት የአመራሩን መናበብ በማሳደግ የበለጠ መስራት የሚቻልበትን ዕድል ይፈጥራል ብለዋል፡፡ በሌማት ትሩፋት በከተማ ግብርና፣ በሙዝና ፓፓያ ክላስተር እንዲሁም በዓሳ ልማት የመጡ ለውጦች በየአካባቢያችን ያልተጠቀምናቸውን ጸጋዎች ለይተን እንድናለማ ያስችላል ነው ያሉት፡፡ በጋምቤላ ክልል የህግና ፍትህ አካላት ጥናትና ምርምር ዳይሬክተር ኡማን ኦጋላ፤ ስልጠናው ወንድማማችነትን በማጠናከር ሀገራዊ ኃላፊነታችንን በብቃት ለመወጣት ያስችለናል ብለዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር እስር በእርስ ለመተዋወቅና ለመተባበር ዕድል እንደሰጣቸው በማንሳት፤ በእስካሁኑ የዜጎችን የልማት ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሰው ተኮር ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም በጥራትና በዓይነት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የግብርና ምርቶችን ለማቅረብ በትጋት መሥራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች እየተከናወኑ የሚገኙ ውጤታማ ስራዎች ብልፅግናን በአጭር ጊዜ ማረጋገጥ የሚያስችሉ ናቸው
Nov 7, 2025 173
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች እየተከናወኑ የሚገኙ ውጤታማ ስራዎች ብልፅግናን በአጭር ጊዜ ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የብልፅግና ፓርቲ የ2018 ዓ.ም ዓመታዊ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና የአመራር አባላቱን አቅም የሚገነቡ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሰሞኑን በአዳማ ከተማ ስልጠና እየተሰጠ መሆኑ ይታወቃል። የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና በሀገሪቱ መሰረታዊ የኢኮኖሚ ዘርፎች በግብርና፣ በቱሪዝም፣ በኢንዱስትሪ እና በከተማ ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮረ እንደነበር ተገልጿል፡፡ ከፍተኛ አመራሮችም ከስልጠናው በተጓዳኝ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ የተገኙት የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር) ብዝሃ ኢኮኖሚ አካሄድን መከተል መጀመራችን ብልፅግናን ለማሳካት ትክክለኛው መንገድ ላይ መሆናችንን ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ይህም የሚፈለገውን ብልፅግና በአጭር ጊዜ ለማረጋገጥ እንደሚጠቅም ገልጸው፤ በግብርናው እና በሌሎችም ዘርፎች እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በብልፅግና ሂደት ውስጥ ገጠሩን አካባቢ ማሸጋገርና ማዘመን ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ መሆኑን አንስተው፤ አርሶ አደሩ ለፍጆታ ከማምረት በዘለለ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ሂደት ሚናው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በገጠር ትራንስፎርሜሽን እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ከራስ ፍጆታ ባሻገር ለገበያ እስከማቅረብ የዘለቀ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ገጠሩን ለኑሮ ምቹ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን መመልከታቸውን የተናገሩት ሚኒስትሯ፤ ገጠሩን ከከተማው ለማስተሳሰር እየተሰሩ ያሉ ስራዎች በጎ ጅማሮዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጄ ዱጉማ በበኩላቸው፤ እንደ ሀገር ትኩረት በተደረጉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት መካሄዱን ተናግረዋል፡፡ በዚህም በገጠር ትራንስፎርሜሽን፣ ኢንዱስትራላይዜሽን፣ የቱሪዝም እምቅ አቅም፣ ከከተማ ልማት ጋር በተያየዙ ብሎም በሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ መወያየታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዛሬው ዕለት በምሥራቅ ሸዋ ዞን ቦራ ወረዳ የተደረገው የልማት ስራዎች ጉብኝት መሬት ላይ ተጨባጭ የሆኑ ስራዎች እየተሰሩ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ በጉብኝቱ የተመለከቱት የዓሳ ልማት ስራ ለህጻናት የተመጣጠነ ምግብ በማቅረብ ብሩህ አዕምሮ እንዲኖራቸውና ምርታማ እንዲሆኑ የሚያደርግ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከዓሣ ልማት ጋር በተገናኘ የተመለከቷቸው ስራዎች የኢትዮጵያ ብልፅግና በአጭር ጊዜ እንደሚረጋገጥ ትልቅ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ጤናማ ማህበረሰብን ለመፍጠር ያስችላል ሲሉም ነው የተናገሩት፡፡
የጋራ ትርክትን በመገንባት የሀገርን ሰላምና አንድነት ለማጽናት የድርሻችንን እንወጣለን-የኪነ ጥበብ እና የሚዲያ ባለሙያዎች
Nov 7, 2025 154
ደሴ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):-የጋራ ትርክትን በመገንባት የሀገርን ሰላምና አንድነት ለማጽናት በሚደረገው ጥረት የድርሻንን እንወጣለን ሲሉ የኪነ ጥበብ እና የሚዲያ ባለሙያዎች ተናገሩ። የደሴ ከተማ አስተዳደር "ሰላም ለሁሉም ሁሉም ለሰላም" በሚል መሪ ሃሳብ ከኪነ ጥበብ ፣ ከሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎችና ከማህበረሰብ አንቂዎች ጋር የውይይት መድረክ አካሄዷል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል ጋሻው ገብሬ በሰጠው አስተያየት እንደገለጸው፣ ዘላቂ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ የጋራ ትርክት መገንባት ላይ መስራት ከሁሉም ይጠበቃል። ለዚህም የኪነ ጥበብ ሙያውን ተጠቅሞ ህብረተሰቡን የሚያስተምሩ በጋራ ትርክት ላይ ያጠነጠኑ ስራዎችን በማቅረብ ሰላምን ለማጽናት በሚደረገው ጥረት የድርሻውን እንደሚወጣ ተናግሯል። የወሎ ባህል ቡድን ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሳሙኤል በላይ በበኩሉ፣ የጋራ ትርክትን የሚያጎለብቱና ሰላምን የሚያጸኑ ሥራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ገልጿል። በዚህም በኪነ ጥበብ ስራዎች ባህሎችን በማስተዋወቅ፣ ሰላምን በመስበክ፣ የእርስ በእርስ ግንኙነቶችን በሚያጠናክሩ ስራዎች ላይ በመሳተፍ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን አክሏል። የኪነ ጥበብ ባለሙያዋ እንግዳወርቅ ካሳሁን ፤ጥበብ እያዝናናችና እያዋዛች ህብረ ብሔራዊ አንድነት ለመፍጠር፣ ሰላምን ለማጽናትና የልማት ሥራዎችን ለማጠናከር ያላትን አቅም ተጠቅመን እንሰራለን ብላለች። የደሴ ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ትግስት አበበ በበኩላቸው፣ የሚዲያና የኮሙኒኬሽን ዘርፉ ለሀገር ሰላም፣ ልማትና አንድነት በቁርጠኝነት መስራት አለበት ብለዋል። በዚህም የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የመረዳዳት፣ የመጠያየቅና የአብሮነት ልምዶች እንዲጎለብቱ እያደረጉ ያለውን ጥረት አጠናክረው እንዲቀጥሉም አሳስበዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰኢድ ካሳው በበኩላቸው፣ ለከተማዋ ዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም በየደረጃው ውይይቶች እየተካሄዱ መሆኑን ጠቁመው አበረታች ውጤትም እየተመዘገበ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ በክልሉ ሰላምን በዘላቂነት ለማፅናት ሚናውን ማጠናከር ይጠበቅበታል-ቢሮው
Nov 7, 2025 141
ባሕርዳር፤ ጥቅምት 28/2018(ኢዜአ)፡- የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ ሃሰተኛና የተዛቡ መረጃዎችን በማጋለጥ በክልሉ ሰላምን በዘላቂነት ለማፅናት ሚናውን ይበልጥ ማጠናከር እንደሚጠበቅበት የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ገለጸ። የተሳሳቱ መረጃዎችን በመከላከል እና እውነተኛ መረጃን በማጣራት ዙሪያ ያተኮረ ስልጠና ለሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን አመራሮች እና ባለሙያዎችን በባሕር ዳር ከተማ ተሰጥቷል። በስልጠናው መድረክ የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ምክትል ሃላፊ ደጀኔ ልመንህ እንዳመለከቱት፤ በክልሉ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ ትክክለኛና ተጨባጭ መረጃ ለማሕበረሰቡ በማድረስ ለዘላቂ ሰላም ግንባታው አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የታሪካዊ ጠላቶች ተላላኪ የሆነውን የፅንፈኛውን ቡድን ጥፋት ሕዝቡ እየተረዳ ተግባሩን ማጋለጥና አምርሮም እየተቃወመው መሆኑን ገልጸዋል። መንግስት ችግሩን በመነጋገር በሰለጠነ አግባብ ለመፍታት ተደጋጋሚ የሰላም ጥሪ ማድረጉን አስታውሰው፤ በዚህም በርካታ የቀድሞ ታጣቂዎች ከተሳሳተ መንገዳቸው በመውጣት መመለሳቸውን አውስተዋል። ለተመላሾችም የተሃድሶ ስልጠና በመስጠት፣ የስራ እድል በመፍጠር፣ መቋቋሚያ ገንዘብና መሰል ድጋፎችን በማድረግ ከማሕበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው ሕይወታቸውን እየቀየሩ እንደሚገኙ አመልክተዋል። መንግስት አሁንም ለሰላምና ንግግር በሩ ክፍት እንደሆነ አንስተው፤ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ በክልሉ ሰላምን በዘላቂነት ለማፅናት አፍራሽና ሃሰተኛ መረጃዎችን በማጋለጥ ሚናውን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሙሉነህ ዘበነ በበኩላቸው፤ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ የመንግስትን የሰላም ግንባታና የልማት አጀንዳዎች በጠራ መረጃ ላይ ተመስርቶ በቅንጅትና በትብብር ማድረስ እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል። የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፉ የክልሉን ዘላቂ ሰላም በመገንባት ሂደት የተዛባና ጥላቻ ተኮር ወሬን በማጋለጥ የላቀ ሚናውን ሊወጣ ይገባል ያሉት ደግሞ የክልሉ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ሃላፊና የመድረኩ ጹሑፍ አቅራቢ አየለ አናውጤ (ዶ/ር) ናቸው። አሁን ላይ ዘመኑ ያመጣቸውን ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ግጭት ቀስቃሽ መረጃዎች በፍጥነት የመሰራጨት ሰፊ እድል መኖሩን ጠቅሰዋል። ባለሙያው ተለዋዋጭና ፈጣን ለሆነው የዘመኑን የመረጃ ስርጭት የሚመጥን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ በመገንባትም በቴክኖሎጂ ታግዞ ትክክለኛ መረጃ በመስጠት ሃሰተኛ መረጃዎችን ማጋለጥ እንዳለበት አመልክተዋል። በመድረኩ የተቋማት የሕዝብ ግንኙነትና የሚዲያ ሃላፊዎች እንዲሁም የዘርፉ ባለሙያዎችና ሌሎችም አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።
የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ በህዳር ወር በአንጎላ ይካሄዳል
Nov 6, 2025 252
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 27/2018(ኢዜአ)፡- ሰባተኛው የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ህዳር 15 እና 16 ቀን 2018 ዓ.ም በአንጎላ ሉዋንዳ ይደረጋል። ጉባኤውን የአንጎላ ፕሬዝዳንት እና በወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር ጆአኦ ሎሬንቾና የአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት አንቶኒዮ ኮስታ በጋራ ይመሩታል። የአፍሪካ ህብረት ከፍተኛ አመራሮች፣ የህብረቱ ሀገራት መሪዎች፣ የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ኡርሱላ ቮን ደር ሌይን እና ሌሎች የአውሮፓ ህብረት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ ወጣቶች፣ የሲቪክ ማህበራትና የንግድ ልዑካን በጉባኤው ይሳተፋሉ። የሁለቱ ተቋማት አጋርነት 25 ዓመታትን ባስቆጠረበት ወቅት የሚካሄደው ይህ ጉባኤ ኢ-ተገማችነት እያደገ በመጣበት ዓለም እና የጂኦ ፖለቲካ ምህዳሮች እየተቀየሩ ባሉበት ጊዜ የሚከናወን መሆኑን የአፍሪካ ህብረት መረጃ ያመለክታል። የተቋማቱ መሪዎች ለባለብዙ ወገን ትብብር፣ አጋርነት እና እየታዩ ላሉ ፈተናዎች የተቀናጀ ምላሽ የመስጠት የጋራ ቁርጠኝነታቸውን እንደሚገልጹ አስታውቋል። ሰላም፣ ደህንነት፣ የኢኮኖሚ ትስስር፣ ንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፣ የአየር ንብረት ለውጥ አይበገሬነት፣ ፍልሰት እና የሰዎች እንቅስቃሴና የሰው ኃይል ልማት ውይይት ከሚደረጉባቸው አጀንዳዎች መካከል ይጠቀሳሉ። የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት የሚወያዩባቸው ጉዳዮች በአጀንዳ 2063፣ በዘላቂ የልማት ግቦችና የአፍሪካ ህብረትና የአውሮፓ ህብረት የ2030 የጋራ ራዕይ ጋር የተቆራኙ መሆናቸው ተመላክቷል። ከዋናው የመሪዎች ጉባኤ አስቀድሞ የወጣቶች እና የሲቪክ እንዲሁም የንግድ ፎረሞች ይካሄዳሉ። በፎረሞቹ ላይ ወጣት መሪዎች፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማትና የግሉ ዘርፍ ባለድርሻ አካላት የሚያነሷቸው ሀሳቦች በመሪዎች ጉባኤ ላይ እንደሚቀርቡ ህብረቱ ገልጿል። ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ እ.አ.አ በ2022 በቤልጂየም መካሄዱ የሚታወስ ነው። በወቅቱ በነበረው ጉባኤ የሁለቱ ተቋማት አባል ሀገራት የ2030 የጋራ ራዕይ ማዕቀፍ ያፀደቁ ሲሆን 150 ቢሊዮን ዩሮ ገደማ የኢንቨስትመንት ማዕቀፍ ይፋ ሆኗል። የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት አጋርነት በይፋ የተጀመረው እ.አ.አ በ2000 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ።