ፍርድ ቤቱ በእነ አቶ ጃዋር ሲራጅ መሀመድ ላይ የቀዳሚ ምርመራ ሂደት እንዲቀጥል ብይን ሰጠ

64

አዲስ አበባ ሀምሌ 30/2012(ኢዜአ) በወንጀል ድርጊት በተጠረጠሩት እነ አቶ ጃዋር ሲራጅ መሐመድ ላይ የቀዳሚ ምርመራ ሂደት እንዲቀጥል ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጠ።

ተጠርጣሪዎቹ በፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት የአራዳ ተረኛ ወንጀል ችሎት ጉዳያቸው ታይቷል።

አቶ ጃዋር ሲራጅ መሐመድ፣ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ አምዛ አዳነን ጨምሮ በመዝገብ ቁጥር 215585 በወንጀል ድርጊት የተጠረጠሩ 14 ግለሰቦች ቀርበዋል።

ተጠርጣሪዎቹ ፍርድ ቤት ዛሬ የቀረቡት ሐምሌ 28 ቀን 2012 ዓ.ም ዐቃቤ ሕግ የቀዳሚ ምርመራ እንዲካሄድ በጠየቀው መሰረት ነው።

በጥያቄው ላይ የተጠርጣሪዎች ጠበቆች አስተያይት እንዲያቀርቡ በተጠየቀው መሰረት ''የቀዳሚ ምርመራ እንዲካሄድ ዐቃቤ ሕግ ያቀረበውን ማመልከቻ በማየት ምላሽ መስጠት እንድንችል ጊዜ ሊሰጠን ይገባል'' ሲሉ ጠይቀዋል።

ችሎቱ ለህዝብ ክፍት ሆኖ በግልጽ መካሄድ ይገባዋል በማለትም ተሟግተዋል።

ደንበኞቻቸው የተጠረጠሩበትን ጉዳይ እንዲያውቁ መደረግ እንዳለበት ጠበቆች ጠይቀዋል።

ዐቃቤ ሕግ በበኩሉ የቀዳሚ ምርመራ ሂደት እንዲካሄድ የጠየቀው ማስረጃ ለማቆየት መሆኑን በመግለጽ፤ መቃወሚያ የሚቀርብበት ጉዳይ እንዳልሆነ ገልጿል።

ችሎቱ ለህዝብ ክፍት ይሁን በማለት ለቀረበውም ክስ ያልተመሰረተና ፍርድ ቤቱ ችሎቱ ክፍት ይሁን ወይም ዝግ ይሁን በሚል የሰጠው ትዕዛዝ ባለመኖሩ ጥያቄው ተገቢነት እንደሌለው አብራርቷል።

ለተጠርጣሪዎች የክስ ጭብጥ ማስረዳት እንደማይጠበቅበትም አመልክቷል።

ዐቃቤ ህግ ለፍርድ ቤቱ ባቀረበው አቤቱታ 15 ምስክሮች በቀዳሚ ምርመራ ሂደት ደህንነታቸው ተጠብቆ ቃላቸውን እንዲሰጡ የጠየቀ ሲሆን፤ ከምስክሮቹ ውስጥ አምስቱ ማንነታቸው ሳይገለጽ ከመጋረጃ ጀርባ ቃላቸውን እንዲሰጡለት ጠይቋል።

በዚህ ጉዳይ ላይ ሃሳባቸውን የገለጹት የተጠርጣሪ ጠበቆች ለምስክሮች የሚደረገው ጥበቃ መቼና በምን ዓይነት ሁኔታ እንደሆነ ሊገለጽ እንደሚገባ አስረድተው፤ ምላሽ ለመስጠት ጊዜ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል።

ማንኛውም ተጠርጣሪ የቀረበበትን ማስረጃ የማየትና ምስክሮችን የመጠየቅ መብት እንዳለው በመግለጽ ከመጋረጃ ጀርባ መሰማት የለበትም በማለት ተከራክረዋል።

ዐቃቤ ሕግ የቀዳሚ ምርመራ እንዲካሄድ የጠየቀው በዋናነት ማስረጃ ለማቆየት መሆኑን በመግለጽ፤ ክርክር የማይካሄድ መሆኑን አስረድቷል።

ግለሰቦቹ የተጠረጠሩባቸው ጉዳዮች በፖሊስ የምርመራ ወቅት መገለጹንም አስታውሷል።

ግራ ቀኙን ያደመጠው ችሎቱ የቀዳሚ ምርመራ ሂደቱ እንዲቀጥል ብይን ሰጥቷል።

ጠበቆች የዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ቃል ሲሰጡ ለመከላከል እንዲያስችላቸው መስቀለኛ ጥያቄ ማቅረብ እንደሚችሉ በይኗል።

ዐቃቤ ህግ ያቀረባቸው አምስት የምስክሮች ማንነት እንዳይገለጽና ከመጋረጃ ጀርባ ቃላቸውን እንዲሰጡ ፈቅዷል።

በመሆኑም የቀዳሚ ምርመራ ሂደቱን ለማካሄድ ዐቃቤ ሕግ ምስክሮቹን ለነሐሴ 4 ቀን 2012 ዓ.ም ይዞ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም