“ደቦ” የተሰኘ የሰዎች ንክኪ መለያ የአንድሮይድ ስልክ መተግበሪያ ይፋ ሆነ

90

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 26/2012(ኢዜ) “ደቦ” የተሰኘ የሰዎች ንክኪ መለያ የአንድሮይድ ስልክ መተግበሪያ ይፋ ሆነ።

የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የኮቪድ-19 በሽታ ስርጭትን ለመከላከል የሚያግዝ “ደቦ” የተሰኘ የሰዎች ንክኪ መለያ የአንድሮይድ ስልክ መተግበሪያ ይፋ ማድረጉን አስታወቀ።

የንክኪ መለያው የአንድሮይድ መተግበሪያ የስልክን የብሉቱዝ ሞገድ በማብራት የራሱን የብሉቱዝ ፕሮቶኮል ተጠቅሞ ከሁለት ሜትር በታች ቅርበት ያላቸውን ሰዎች በስልካቸው ላይ ያለውን መለያ ቁጥር እንዲለዋወጡ የሚያደርግ ነው ተብሏል።

ይህም ቁጥር በሁለቱም ስልኮች ላይ በምሥጢር የሚቀመጥ ሲሆን፣ ንክኪን የሚለየው ቡድን በበሽታ የተያዘውን ሰው ስልክ በመጠቀም ከደቦ ላይ ድብቅ ቁጥሮቹን በመለየት ከተያዘው ሰው ጋር ቅርበት ወይም ንክኪ ሊኖራቸው የሚችሉ ሰዎችን በመለየት ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ብሎም ክትትል እንዲደረግላቸው ያደርጋል።

“ደቦ” መተግበሪያ አንድ ግለሰብ የቀን ውሎውን መመዝገብ የሚያስችለው መሆኑም ተመልክቷል።

መተግበሪያው የአንድሮይድ ስልክ የማይጠቀሙ በአቅራቢያችን ይበልጥ ተጋላጭ እና ንክኪ ያላቸው ሰዎች በየዕለቱ ዲያሪ ላይ ስልካቸውን፣ ስማቸውን እና ጾታቸውን በመመዝገብ በቀላሉ እንዲለዩ ማድረግ እንደሚችልም ተገልጿል።

ማኅበረሰቡ ደቦ መተግበሪያን https://debo.ephi.gov.et ከሚለው ድረ ገጽ በመውሰድ በስልኩ ላይ በመጫን የኮቪድ-19 በሽታ ስርጭትን እንዲከላከል ኢንስቲትዩቱ ጥሪ አቅርቧል።

መተግበሪያውን ለመጠቀም ተጠቃሚው ስልኩ ላይ ከጫነ በኋላ ተያይዞ የቀረበውን ቅጽ ኢንተርኔት ክፍት በማድረግ ሞልቶ መጨረስ እንደሚገባም አሳስቧል።

የአንድሮይድ 9 እና 10 ተጠቃሚዎች ግን የብሉቱዙን መለያ ከቅንብር (setting) ውስጥ ወስደው መሙላት እንደሚችሉ ከኢንስቲትዩት ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም