በኢትዮጵያ አንድ የ9 ወር ህጻንን ጨምሮ ተጨማሪ ስምንት ሰዎች የኮሮናቫይረስ ተገኘባቸው

126

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 29/2012( ኢዜአ) በኢትዮጵያ ባለፉት 24 ሰዓት የላቦራቶሪ ምርመራ ከተደረገላቸው 264 ሰዎች ውስጥ 8 ሰዎች የኮሮናቫይረስ እንደተገኘባቸው ተረጋገጠ።


ቫይረሱ ከተገኘባቸው ሰዎች መካከል አንድ የዘጠኝ ወር ህጻን የተያዘ ሲሆን እናቱም ቫይረሱ ተገኝቶባታል። 

የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር ሊያ ታደሰ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በ24 ሰዓታት ውስጥ ምርመራ ከተደረገላቸው ሰዎች መካካል አንዱ ኤርትራዊ ሲሆን ቀሪዎቹ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ናቸው።

ይህም በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎችን ቁጥር 52 አድርሶታል ነው ያሉት።

በበሽታው መያዛቸው ከተረጋገጠ ስምንቱ ሰዎች መካከል አምስቱ ከዱባይ የመጡና በለይቶ ማቆያ ውስጥ ክትትል ሲደረግላቸው የነበሩ ናቸው።

ከእነዚህም ውስጥ አንድ የዘጠኝ ወር ህጻንና ወላጅ እናቱ ይገኙበታል።

አንድ የ25 ዓመት ሴት ኢትዮጵያዊት ከታይላንድ መጥታ በለይቶ ማቆያ ክትትል ስታደርግ የነበረች ሲሆን፤ አንድ የ19 ዓመት ኢትዮጵያዊ የውጭ አገር ጉዞ ታሪክ የሌለው ሲሆን የንክኪ ሁኔታውም በመጣራት ላይ ይገኛል ብለዋል።

ሌላኛዋ የ30 ዓመት ሴት ኤርትራዊት ስትሆን ከእንግሊዝ ለንደን መጥታ በአዲስ አበባ በለይቶ ማቆያ ክትትል እያደረገች የምትገኝ ናት።

በአዲስ አበባ እና በሌሎች የክልል ከተሞች የኮሮናቫይረስ የላቦራቶሪ ምርመራ አቅም እየጨመረ መጣቱንም ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች መካከል አንድ ግለሰብ በጽኑ ህሙማን ማቆያ ይገኛሉ።

አራቱ ያገገሙ ሲሆን፤ ሁለቱ በቫይረሱ ምክንያት ህይወታቸው ማለፉ ይታወሳል።

ሌላ ሁለት ግለሰቦች ደግሞ ወደ ሀገራቸው ተሸኝተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም