6 ሚሊዮን ህፃናትን ከመቀንጨር ለመታደግ እየተሰራ ነው

119

ዋግ-ህምራ የካቲት 19/2012 (ኢዜአ) የሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነት ፕሮግራምን ውጤታማ በማድረግ በመቀንጨር የተጠቁ 6 ሚሊዮን ህፃናትን ለመታደግ ከ477 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ።

የሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነት ፕሮግራም ውጤታማ በማድረግ በመቀንጨር የተጠቁ 6 ሚሊዮን ህፃናትን ለመታደግ ከ477 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦ እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ።

የሰቆጣ ቃል ኪዳን የሙከራ ምእራፍ ትግበራ የ2012 ዓ.ም የመጀመሪያ ግማሽ አመት አፈጻጸም ግምገማ በዋግ 

ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ሰቆጣ ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡

በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የእናቶች እና ህፃናት ጤና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶክተር መሰረት ዘላለም በግምገማ  መድረኩ ላይ  እንደተናገሩት  በኢትዮጵያ የምግብና የስርአተ ምግብ ዋስትና ባለመረጋገጡ በርካታ ህፃናት  ለመቀንጨር ተጋልጠዋል።

በአሁኑ ወቅት በሃገሪቱ በስርአተ ምግብ እጥረት ምክንያት እድሜያቸው ከአምስት አመት በታች ያሉ 6 ሚሊዮን  ህፃናት ለመቀንጨር የተጋለጡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በተለይም በተከዜ ተፋሰስ ላይ በሚገኙ የአማራና የትግራይ ክልሎች በ40 ወረዳዎች እድሜያቸው ከሁለት አመት  በታች ያሉ ህጻናት በአሳሳቢ የመቀንጨር ችግር ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡

በስርአተ ምግብ እጥረት የቀነጨሩ ህፃናት እድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በትምህርት አቀባበላቸው ፣ አካላዊና  አዕምሮአዊ እድገት ላይ ተፅእኖ በማሳደር ለራሳቸውም ሆነ ለሃገራቸው አስተዋፅኦ እንዳያበረክቱ ያደርጋቸዋል።

የችግሩን አሳሳቢነት በመረዳትም የሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነትን በመተግበር በሃገር አቀፍ ደረጃ የመቀንጨርን ችግር በ2022 ዓ.ም ዜሮ ለማድረስ ግብ ተጥሎ እየተሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል።

ባለፉት ሁለት አመታትም መንግስት እና አጋር ድርጅቶች የተለያዩ ተግባራት ማከናወናቸውን ጠቅሰው፤ በተያዘው  በጀት አመት የሰቆጣ ቃል ኪዳንን ግብ ለማሳካት 477 ሚሊዮን ብር በጀት ተመድቦ እየተሰራ መሆኑን  አስታውቀዋል።

በተመደበው በጀትም በፍጥነት ለውጥ በሚያመጡ የግብርና፣ የትምህርት፣ የእናቶችና ህጻናት ጤና አጠባበቅ፣ በውሃ አቅርቦት፣ በመንገድ መሰረተ ልማት ግንባታና ሌሎች ልማቶች ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ይገኛል።

የተመደበው ሃብት ለታለመለት አላማ እንዲውልም የሚመለከታቸው አስፈፃሚዎች በቅንጅት ሊሰሩ  እንደሚገባ ዶክተር መሰረት አሳስበዋል።

በሙከራ ትግበራ ላይ የነበረው ፕሮግራም ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ሙሉ ትግበራ ለማሸጋገር የ15 ዓመት  ስትራቴጅክ እቅድ መነደፉን ጠቅሰዋል።

በፌደራል እና በክልል መስሪያ ቤቶች የሚፈፀሙ ተግባራትን መረጃን መሰረት ያደረገ የውሳኔ አሰጣጥ ስርአት 

በመዘርጋቱ የፕሮግራሙን የትግበራ ምእራፍ ስኬታማ ያደርገዋል ያሉት ደግሞ  የሰቆጣ ቃል ኪዳን የፌደራል 

ፕሮግራም ማስፈፀሚያ ክፍል አስተባባሪ ዶክተር ሲሳይ ሲናሞ ናቸው፡፡

ፕሮግራሙ በዚህ ዓመት በአማራና በትግራይ ክልሎች ለሚገኙ 40 ወረዳዎች የትምህርት፣ ጤና፣ ግብርና እና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን ለማስፋፋት የሚያስችል በጀት ተመድቦ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል ።

ባለፉት ስድስት ወራት የመረጃ ስርአቱን ለማጠናከር ቴክኖሎጂን መሰረት ያደረገ የስልክ መሰረተ ልማት 

በማስፋፋትና መሰረተ ልማቱ ባልተዘረጋላቸው 721 ቀበሌዎች ደግም በሳተላይት አማካኝነት ተደራሽ የማድረግ ስራ

 እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል ።

ፕሮግራሙ በሙከራ ትግበራ ምእራፉ ላይ በፍላጎትና በሃብት አቅርቦት አለመመጣጠን እንዲሁም የቀበሌዎች

 የመንገድ መሰረተ ልማት ያለመሟላት ችግር አሉታዊ ተፅእኖ ማሳደሩን ተናግረዋል ።

የዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ዋና አስተዳዳሪ አቶ በሪሁን ኪዳነ ማርያም በበኩላቸው የሰቆጣ ቃል ኪዳን 

ባከናወናቸው የሙከራ የትግበራ ምእራፎች በብሄረሰብ አስተዳደሩ የሚያበረታታ ለውጥ እየተመዘገባበመሆኑን  ተናግረዋል ፡፡

ባለፈው አመት በቃል ኪዳኑና በሌሎች አጋር አካላት በተደረገ ጥረት ከ300 በላይ አዲስ የመማሪያ ክፍሎችን ወደ ቋሚ ክፍሎች አንዲያድጉ መደረጉን  በማሳያነት አንስተዋል፡፡

በዘንድሮው አመትም በቃል ኪዳኑ በተደረገ የበጀት ድጋፍ በዳስ ይማሩ የነበሩ ህፃናትን በክፍል እንዲማሩ ለማድረግ የ33 የመማሪያ ክፍሎች ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ዋና አስተዳዳሪው  ተናግረዋል፡፡  

"በመንግስት እና በአጋሮች ርብርብ የሰቆጣ ቃል ኪዳንን ግብ ለማሳካት የእድገት ክትትል ውጤትን እንደ ጠቋሚ 

እንጠቀማለን" በሚል መሪ ቃል ለሁለት ቀናት እየተካሔደ ባለው የግምገማ መድረክ ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችና ከአማራና ትግራይ ክልል የተውጣጡ የስራ ሃላፊዎች  ተሳታፊ ሁነዋል፡፡  

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም