ኢትዮጵያ የመጀመሪያዋን ሳተላይት ወደ ህዋ አመጠቀች

200

ኢዜአ፤ታህሳስ 10/2012 ኢትዮጵያ የመጀመሪዋ የመሬት መመልከቻ 'ETRSS-1' የተሰኘችውን ሳተላይት ወደ ህዋ አምጥቃለች።

ማይክሮ ሳተላይቷ ዛሬ እንድትመጥቅ የተወሰነው በስፍራው ያለው የአየር ጸባይ ምቹ መሆኑ በመረጋገጡ ነው። የሳተላይቷ መምጠቅ ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ከስፔስ ቴክኖሎጂ ጋር የመተዋወቋ ማረጋገጫ ነው።

ይችው 72 ኪሎ ግራም የምትመዝነው ሳተላይት የመጠቀችው ከቤጂንግ 400 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው ታይዱዋ ከተባለ የማምጠቂያ ጣቢያ ነው።  ሳተላይቷ  700 ኪሎ ሜትር በመምጠቅ በሰላሳ ደቂቃ ውስጥ በህዋ ውስጥ ቦታዋን እንደምትይዝ ታውቋል።

ዛሬ ሳተላይቷ የመጠቀችው 'ሎንግ ዋይ ፎር ቢ' በተሰኘው ሮኬት እንደሆነ ተጠቁሟል።

ስኬታማ በሆነው መንገድ የመጠቀችው ሳተላይት ኢትዮጵያ ለግብርና፣ ለደንና አየር ንብረት ጥበቃ፣ ለማዕድን፣ ለተፈጥሮ ሀብት ጥናትና መረጃ ለመሰብሰብ፣ መሰረተ ልማት ለመዘርጋትና ለመጠበቅ እምደምትገለገልበት መረጃዎች ያመለክታሉ።

ኢትዮጵያ የህዋ ሳይንስን በተመለከተ በ1950 ዎቹ ሀሳቡ የነበራት ቢሆንም እንደዛሬው ከ70ዎቹ አገሮች አንዷ የሚያደርጋትን ስኬታማ ተግባር ለማከናወን ሳይቻል መቅረቱን ነው መረጃዎች የሚያረጋግጡት።

የሳተላይት ግንባታው የተካሄደው ከቻይና ጋር በመተባበር ሲሆን፤ በዚህም 20 የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን ኢንጅነሮች ተሳትፈዋል።

በቀጣይም ሳተላይቷን የመቆጣጠርና መረጃዎችን የመሰብሰብ ስራው ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን መሃንዲሶች ይከናወናል።

ኢትዮጵያ ወደፊት በኮሙኬሽንና ብሮድካስትም ሳተላይት ለማምጠቅና በምስራቅ አፍሪካ ከሳተላይት አገልግሎት የውጭ ምንዛሬ የምታገኝበትን አጋጣሚ ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ።

ወደፊትም ኢትዮጵያ በራሷ ዲዛይን ብቻ ሳተላይት ለማምረትና ስርዓት ለመፍጠርም  የተለያዩ ተግባራት እያከናወነች ነው።

በቻይና ለተከናወነው ሳተላይት የማምጠቅ መርሃ ግብር ላይ ለመሳተፍ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት እንዲሁም ከጋዜጠኞች የተውጣጣ ልዑክ በስፍራው ተገኝቷል።

በተጨማሪም ከባህር ወለል በላይ 3200 ሜትር ከፍታ ላይ በሚገኘው እንጦጦ ኦብዘርቫቶሪ ምርምር ማዕከል በሚካሄደው መርሃ ግብር ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ኬሪያ ኢብራሂም፣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ በኢትዮጵያ የቻይናን አምባሳደር ጨምሮ የተለያዩ አገሮች አምባሳደሮችና ታዋቂ ሰዎች ተገኝተዋል።

የስፔስ ሳይንስ ቴክኖሎጂም የቅንጦት ሳይሆን ኢትዮጵያ ተወዳደሪና ውጤታማ እድገት ለመፍጠር አጋዥ ዘርፍ መሆኑን አብራርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም