ኢህአዴግን ህብረ ብሔራዊ ፓርቲ ለማድረግ የተካሄደው የዝግጅት ሥራ መጠናቀቁ ተገለጸ

86
ኢዜአ ህዳር 02 ቀን 2012 ዓ.ም ኢህአዴግን አጋር ድርጅቶቹን በማካተት ህብረ ብሔራዊ ፓርቲ ለማድረግ የተካሄደው ዝግጅት መጠናቀቁን  የኢህአዴግ ምክር ቤት አስታወቀ። የግንባሩ አባላት፣ ሕዝቡና የመንግስት ሠራተኛው ለውህደቱ ተግባራዊነት የማይተካ ሚናቸውን እንዲወጡ ምክር ቤቱ ጥሪ አቅርቧል። የኢትዮጵያ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር /ኢህአዴግ/ ላለፉት 29 ዓመታት ከአራት ፓርቲዎች ጋር ግንባር ፈጥሮ ሀገሪቱን ሲመራ መቆየቱ ይታወሳል። በሀገሪቱ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተካሄደው ሕዝባዊ እምቢተኝነት በመጣው ለውጥ አማካኝነት ግንባሩን ወደሀገራዊ ህብረ ብሔራዊ ፓርቲነት ለማምጣት በግንባሩ ጽሕፈት ቤት በኩል የዝግጅት ሥራ ሲያከናውን ቆይቷል። ውህደቱን ከግንባሩ አባል ድርጅቶች ባሻገር ላለፉት ዓመታት ከግንባሩ ጋር በአጋርነት ሲሰሩ የቆዩትንም ሌሎች ፓርቲዎች የሚያካትት መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት የውህደቱን የዝግጅት ሥራ አስመልክቶ የግንባሩ ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መለሰ አለሙን አነጋግሯል። አቶ መለስ አለሙ የኢህአዴግን የውህደት ሂደት አመጣጥን የሚገልጹት የሕዝብን የመለወጥ ፍላጎትና የልማት ጥያቄን ከመመለስ አኳያ ነው። ውህደቱ ሕዝባዊ መሠረት የሌለው ነው በሚል በአንዳንድ አካላት የሚቀርበውን አስተያየት አቶ መለስ አይቀበሉትም። እነዚህ አካላት ለውጡ እንዳይመጣ በየጊዜው መሰናክል ሲያስቀምጡ የቆዩ ናቸው የሚሉት የጽሕፈት ቤት ኃላፊ፤ የውህደቱ አስፈላጊነት ከድርጅቱ 5ኛ ጉባኤ ጀምሮ ሲታሰብበት የመጣ አቋም መሆኑን ያብራራሉ። የድርጅቱ ውህድ መሆን የሀገር መሠረታዊ አንድነትን በመፍጠር በጋራ መልማትን ከማምጣት ባለፈ አባላቱ በሀገራዊ ጉዳይ ላይ ወጥ አቋምና አስተሳሰብ እንዲኖራቸው እንደሚያስችልም አቶ መለስ አለሙ ያስረዳሉ። የኢህአዴግ አባልና አጋር ድርጅቶችን በማዋሀድ ሀገራዊ ራእይ ያለው ፓርቲ የመፍጠሩ ዝግጅት ሥራ  መጠናቀቁን አቶ መለሰ ያብራራሉ። በመሆኑም ለሚፈጠረው ሀገራዊ ፓርቲ እውን መሆን የግንባሩ አባላት፣ የመንግሥት ሠራተኛውና ሕዝቡ እንደወትሮ ሁሉ ገንቢ ሚናቸውን እንዲወጡ ኃላፊው ጥሪ አቅርበዋል። ውህደቱ ከሕወሓት በቀር በሌሎቹ የግንባሩ አባላት ይሁንታ ማግኘቱን የብሔራዊ ድርጅቶቹ አመራሮች በመገናኛ ብዙሃን መግለጻቸው ይታወቃል። በዚህ ሳምንት የሚካሄደው የግንባሩ የሥራ አስፈጻሚ ስብሰባ ላይ የውህደቱ ጉዳይ ዋና አጀንዳ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም