የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ የኖቤል ሽልማት የሁሉም ኢትዮጵያውያን ነው - የኃይማኖት አባቶች

50
አዲስ አበባ ጥቅምት 9 /2012 የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ የኖቤል ሽልማት የሁሉም ኢትዮጵያውያን መሆኑን በዋሽንግተን ዲሲ ኢትዮጵያውያን የኃይማኖት አባቶች ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የ2019 የኖቤል ተሸላሚ መሆናቸውን አስመልክቶ በዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ ኢምባሲ የደስታ መግለጫ ፕሮግራም ተካሂዷል። በዝግጅቱ የተገኙ የኃይማኖት አባቶች ባስተላለፉት መልዕክት ሽልማቱ የሁሉም ኢትዮጵያውያን በመሆኑ ከዚህ ዕውቅና በመነሳት ለላቀ አንድነትና ብልፅግና መነሳት አለብን ብለዋል። ኢትዮጵያውያን ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጎን በመቆም ለጀመሯቸው አገራዊ እቅዶችና የለውጥ ሂደት መሳካት የበኩላቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል። በአሜሪካ ዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ አምባሳደር ፍፁም አረጋ በበኩላቸው "ሽልማቱ መላ ኢትዮጵያውያንን ያኮራና ከተባበርን የማናስመዘግበው ስኬት እንደሌለ አይነተኛ ማሳያ ነው" ብለዋል። በዋሽንግተን ዲሲ የደስታ መግለጫ ኘሮግራም በማዘጋጀት ላስተባበሩ አካላትም አምባሳደር ፍፁም ምስጋና አቅርበዋል። የዋሽንግተንና አካባቢው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ተወካዮች፣ የዳያስፖራ አባላትና ኤምባሲው የዝግጅቱ አስተባባሪዎች መሆናቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጽሕፈት ቤት አስታውቋል።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም